Author name: David Yeshua

የሥላሴ ሥነ አመክንዮአዊ ችግር(LPT)

የሥላሴ አስተምህሮ በተለያዩ ሰዎች በተለያዩ ዘመናትም ትችት ሲደርስበት መስማት የተለመደ ነው። ይህንንም ትምህርት በሰዎች አእምሮ ዘንድ ፈጽሞ መረዳት የማይቻልና በተለይም “አምላክ/God/” የሚለውን ቃል በተለያዩ አይነት በመጠቀም በሥነ አመክንዮ ዘንድ መሠረታዊ ችግር እንዳለበት ለማሳየት ይሞክራሉ። ሙግቱ እንዲህ ይቀርባል፦ 1) ክርስቲያኖች አብ አምላክ ነው፣ ወልድ አምላክ ነው፣ መንፈስ ቅዱስ አምላክ ነው ይላሉ። 2) ነገር ግን “አምላክ” የሚለው ቃል በአንድ ጊዜ አብን፣ ወልድን እንዲሁም መንፈስን የሚያመለክት ከሆነ አንድን ምንነት ያለውን አምላክ በቋሚነት ሊያመለክት አይችልም። 3) ስለዚህ ይህ አስተምህሮው ከአመክንዮአዊ ወጥነት ይልቅ አሻሚ የሆነ ግራ አጋቢ ትርጉም ላይ እንዲሆን ያደርገዋል። መልስ ይህ ሙግት መሠረት ያደረገው እኛን(ክርስቲያኖችን) “አምላክ” የሚለውን ቃል የተለያዩ አካላትን በተለያየ መንገድ መገለጫ እንደሆነ በማመልከት እንደምንል አድርጎ ሙጉቱን በሥሑት ነጥቦች ላይ ገንብቶ የጀመረ ነው። ማለትም “አምላክ” አብን በአንድ መንገድ፣ ወልድን በሌላ ፣ እንዲሁም መንፈስ ቅዱስን በሌላ እንደማለት ነው። ነገር ግን ይህ አይነቱ መረዳት በሥላሴ የአምላክነት ባሕርይ ወይም “ግጻዌ መለኮት” መረዳት ውስጥ የማያታወቅ ነው። ታዲያ አምላክ ማለት ግን በኑባሬው ያለማቋረጥ አንድ፣ የማይከፋፈል መለኮታዊ ማንነትን የሚያመለክት መለኮታዊ ባህርይ የሚል ቃል ነው። ስለዚህ ክርስቲያኖች “አብ አምላክ ነው”፣ “ወልድ አምላክ ነው” እንዲሁም “መንፈስ አምላክ ነው” ሲሉ የአምላክነት ባህርይን ያለውን አካላቶቹ አሏቸው በዚህም እያንዳንዱ አካል ያንን የመለኮትነትን ባህርይ ሙሉ በሙሉ ይጋራሉ ማለታቸው ነው። ይህም አንድ አምላክ ብቻ አለ ሲባል፣ አንድ ምንነት እንዳለ እያረጋገጡ ነው። አንዱ አምላክ በሦስት አካል የተገለጠ ነው ሲሉ ደግሞ አንድ አምላክ በአካል ሦስት ነው እያሉ ነው። አብ፣ ወልድ እና መንፈስ አንድ አምላክ ናቸው ሲሉ እያንዳንዱ አካል መለኮታዊ ባህርይ እንዳለው እያስረገጡ ነው። ስለዚህ፣ ከላይ በሥላሴ ላይ በተነሳው የሶስቱ ነጥብ ሙግቶች፣ “አምላክ” የሚለውን ቃል ውይይት ከመገባቱ በፊት ከተብራራ፣ የሚመጣውን የትኛውንም ጥያቄ ይመልሳል ማለት ነው።

የሥላሴ ሥነ አመክንዮአዊ ችግር(LPT) Read More »

ኑ መጽሐፍ ቅዱስን እንተዋወቀው

ሰላም። በመጀመሪያ ከእኛ ጋር መጽሐፍ ቅዱስን ለማንበብ ዝግጁና ፍቃደኛ በመሆናችሁ እግዚአብሔርን እናመሰግናለን። ምናልባት ይህን በእጃችሁ ያለውን መጽሐፍ አዲስ እና እንግዳ ሆኖባችሁ ይሆናል። ዛሬ በዚህ ጽሑፍም በእጃችሁ የሚገኘው መጽሐፍ ቅዱስ የሚለው መጽሐፍ ምንድነው የሚለውን በአጭሩ የምንተዋወቅ ይሆናል። ክርስቲያኖች 66ቁጥሮች ርዝማኔ ያላቸው መጻሕፍ አላቸው። እነዚህም መጻሕፍትበሁለት ክፍል ይቀመጣሉ። እነርሱም ብሉይ ኪዳን እና አዲስ ኪዳን በማለት ይከፈላሉ። ብሉይ ኪዳን 39 አዲስ ኪዳን ደግሞ 27 መጻሕፍትን ይዘዋል። መጽሐፍ ቅዱስ የሚለው ቃል የእንግሊዝኛው አቻ ትርጉም “ባይብል” የሚለው “ቢብሊያ” ከሚለው የጽርእ(የግሪክ) ቃል የመጣ ሲሆን “መጻሕፍት” ማለት ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ በአንድ ግለሰብ እንዲሁም በጥቂት ዓመታት ውስጥ የተጻፈ መጽሐፍ ሳይሆን፣ በብዙ መቶ ዘመናት ውስጥ በተለያዩ ቋንቋዎች ከ40 በላይ ጸሐፊያን ያሉትና በ1500 ዓመታት ውስጥ የተጻፉ የተለያዩ መጻሕፍት ስብስብ ነው፡፡ በእርሱም ውስጥ እግዚአብሔር በቀጥታ ከህዝቡ ጋር ይነጋገራል፣ በሌላ ጊዜ ደግሞ በቅዱሳን ሰዎች ሐሳብና ቃል አማካኝነት ሲናገር፣ ከሁሉም በላይ ደግሞ በዘመን መጨረሻ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ተግልጦ ተናግሮናል። በመጽሐፍ ቅዱስ ምሑራን የጊዜ አመዳደብ መሰረት የመጀመርያው ክፍል ከክርስቶስ ልደት በፊት በ1400 ዓ.ዓ. አካባቢ እንደሆነና የመጨረሻው ደግሞ ከክርስቶስ ልደት በኋላ በ90 ዓ.ም. አካባቢ እንደተጻፈ ይታመናል። መጽሐፍ ቅዱስን ስናነብ ማወቅ ካሉብን ልዩ ሁኔታዎች መካከል መጽሐፍ ቅዱስ እንደ ቁርአን እና ሌሎች አይነት መገለጥ እንዳልሆነ ነው። ይህን ለመረዳት ጳውሎስ ለመንፈሳዊ ልጁ ለጢሞቴዎስ በላከው 2ኛ ጢሞቴዎስ 3፥16-17 እንዲህ ሲል ይናገራል፦ “የእግዚአብሔር ሰው ፍጹምና ለበጎ ሥራ ሁሉ የተዘጋጀ ይሆን ዘንድ፥ የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበት መጽሐፍ ሁሉለትምህርትና ለተግሣጽ ልብንም ለማቅናት በጽድቅም ላለው ምክር ደግሞ ይጠቅማል።” በዚህ ክፍል ላይ ጳውሎስ የእግዚአብሔርን ቃል፣θεόπνευστος “ቴኦፕኔውስቶስ” መሆኑን ሲናገር የቃሉ ፍቺ θεό “ቴኦ” ማለት “እግዚአብሔር” እና πνευστος “ፕኔውስቶስ” ማለትም “መንፈስ” ከሚሉ ሁለት የጽርእ ቃል የተገኘ ነው፤ በአንድ ላይ ሲነበቡም “እስትንፋሰ እግዚአብሔር” የሚል ነው። ታዲያ መጽሐፍ ቅዱስ ሁሉ በእግዚአብሔር መንፈስ እስትንፋስ የተጻፈ ነው፤ የሰዎችን ልብ ሁሉ የሚቀይር እንዲሁም በእምነት የሚያነብ የእርሱን ድምፅ ይሰማል። በግልጽ ልብና አእምሮ ካነበብነው፣ እግዚአብሔር እኛ በማናቀው መንገድ ሲናገረን እንገኛለን። ስለዚህ ይህ የያዛችሁት መጽሐፍ ሌሎች ጋር እንዳለ አይነት መጽሐፍ እንዳልሆነ በእነዚህ መንገዶች ትረዳላችሁ። የመጻሕፍቱ ዝርዝር # መደቦች የመጽሐፍቱ ብዛት መጻሕፍቱ 1 የሙሴ ሕግ (ፔንታቱክ) 5 ዘፍጥረት – ዘዳግም 2 የታሪክ መጻሕፍት 12 እያሱ – አስቴር 3 ቅኔ/ግጥም 5 እዮብ – መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን 4 አበይት ነብያት 5 ኢሳይያስ – ዳንኤል 5 ደቂቅ ነብያት 12 ሆሴዕ – ሚልኪያ       ➡ አጠቃላይ ብሉይ ኪዳን 39 6 ወንጌላት 4 ማቴዎስ – ዮሐንስ 7 የታሪክ መጽሐፍ 1 ሐዋርያት ሥራ 8 የጳውሎስ መልእክታት 13 ሮሜ – ፊልሞና 9 አጠቃላይ መልእክታት 8 ዕብራውያን – ይሁዳ 10 ራዕይ(አቡቀለምሲስ) 1 ራዕይ ➡ አጠቃላይ አዲስ ኪዳን 27 ➡ ጠቅላላ ድምር 66 መጽሐፍ ቅዱስ በአጭሩ የመጽሐፉ ዋና ዋና መልእክቶች፦ በኦሪት ዘፍጥረት ምዕራፍ 1 ላይ ዓለምን የፈጠረ እግዚአብሔር እንደሆነ ገልጾ በማሳየት ይጀምራል። በዚህም እግዚአብሔርም ፍጥረታትን በስድስት ቀን እንደፈጠረ በሰባተኛው ቀን እንዳጠናቀቀ እንመለከታለን። በዚህም ውስጥ “ሰውን በመልካችን እንደ ምሳሌአችን እንፍጠር” በማለት ሰው የሚለውን ከፍጥረቱ ሁሉ መካከል ልዩ አድርጎ እንደሰራው፣ ስማቸውንም አዳም እና ሔዋን እንደነበሩ እንመለከታልን። በዚህም የፍጥረት መጽሐፍ ላይ የምንረዳው የዓለማትና የእኛ ሠሪ አንዱ እግዚአብሔር ብቻ እንደሆነ አስተዋውቆ ይጀምራል። ነገር ግን ብዙም ሳይቆይ በቅድስና የተመሰገነውን አምላክ አዳምና ሔዋን ኃጢአት ሰርተው እንዳሳዘኑት በዚህም ከእግዚአብሔርም ጋር የነበራቸው ግንኙነት ሲያጡ እንመለከታለን። ከዚያም እግዚአብሔርም በሙሴ በማስነሳት(ዘፀአት 7) በእርሱ በኩል አሥርቱን ትእዛዛት(በዘፀአት 20) እንዴት እንደሰጣቸው እንመለከታለን። በታሪክ መጻሕፍት ውስጥ የኪዳኑ ሕዝብ ኪዳን ከሌላቸው ጣኦት አምላኪያን ጋር የነበራቸውን ውጣ ውረድና የእግዚአብሔርን ፍቅሩ ጽድቁን ባደረጉት የቁጣው ፀሐይ ደግሞ ባልፈለጉት ላይ እንደወጣች በሰፊው ተከትቦ እናገኛለን። በእያንዳንዱ ታሪኮችን ውስጥ የምንገነዘበው ነገር እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ያለው የታመነ ፍቅሩ ነው፤ እርሱም በደንዳናው ሕዝበ እስራኤል ላይ ምን ያህል ታጋሽ የሆነ ፍቅር እንዳለው በስፊው ተቀምጦልናል። ለምሳሌ፦ እንደ ኖኅ፣ አብርሃም፣ ሙሴ፣ ኢዮብ፣ ዳዊት እና ሌሎች ያሉ የተወሰኑ ሰዎችን በልዩ መንገድ ጠርቶ ይህ ኃያል አምላክ በየዘመናቱ ፍቅሩን ሲገልጥ እናገኘዋለን። እነዚያ የመረጣቸው የኪዳኑ ሕዝብ በኋላም ከአመጻቸው የተነሳ ለእግዚአብሔር ሕግ መታዘዝ እንዳቃታቸው ስለዚህም እግዚአብሔር በመጨረሻው ዘመን የሰው ልጆች ያፈረሱትን የድሮውን ኪዳን ለመፈጸም እና አዲስን ኪዳን ከህዝቡ ጋር ለማቆም አንድያ ልጁን የላከው። ይህ አዲሱ ኪዳን ግን በደካማ የሰው ልጆች ሥራና ታዛዥነት ላይ የተመሰረተ ሳይሆን፣ በሰማያዊው አዳኝ፣ በዘላለማዊው ቃል በሆነው በመሲሕ ላይ ነው። ይህ መሲሕ በብሉይ ኪዳን ዘመን ጌታችን ኢየሱስ ከድንግል ከመወለዱ ከ700 ዓመት በፊት በነብዩ ኢሳይያስ ላይ ተነግሮለታል። አሁን የትንቢቱ ፍጻሜው ቀረበና እርሱ ራሱ በትልቁ የሮም ግዛት እጅጉን ደሳሳና አናሳ በሆነች ቤት የተወለደ ሆኖ መጣ።(ዮሐንስ 1፥14) አዎን ከላይ እንዳልነው እግዚአብሔር ኃያልና የከበረ ነው፣ ነገር ግን እርሱን እንድናውቀው ግን የባሪያን መልክ ያዘ።(ፊልጵስዩስ 2) የክርስቶስን ሕይወትና አገልግሎት ስናነብ ሳለ በአእምሯችን ሥሑት ትርጓሜ እንዳይፈጠር ሥነመለኮታችንን የተቃኘ መሆን አለበት። በዚህም የሚያግዟችሁን ጥሩ መጋቢያን መፈለግ ጥሩ ነው። አንዳንድ መናፍቃን አምላክ አይደለም ይልቅ ሰው ብቻ ነበር በማለት ሊያስቱ ይሞክሩ ይሆናል። በዚህም ትምህርት ንፋስ ተውስደን “ኢየሱስ ሰው ብቻ ነበር” ካልን፣ ሙሉ በሙሉ እንስታለን። “ሰው አይደለም አምላክ ብቻ ነበር” ካልንም ሰውነቱን ክደናልና ከሃዲያን እንባላለን። የነገረ ክርስቶስ ጥናት ስፊ ውቂያኖስ ነው። ይህንንም ሐሳብ መምህራን ሲገልጡ “…ጥናቱም ልክ ቀጭን ምላጭ ላይ እንደመራመድ ማለት ነው። በግራ ብንወድቅ አውጣኬ አለ። በቀኝ የወደቅን የሆንን ከሆነ ድግሞ ንስጥሮስ አለ…” በማለት ያስቀምጣሉ። ታዲያ ነገረ ክርስቶሳችን ጥናቱ ያልተቃኘ ከሆነ መርማሪው እንዳይወድቅ ይፍራ። ጥሩ አንባቢ ክርስቲያን ግን በቀጭኗ ምላጭ ላይ በቀስታ ይራመዳል። ስለዚህ በዚህን መጽሐፍ ቅዱስን ጥናት ወቅት አውዱን ያልሳተ ትርጓሜ መጠቀም፣ ተዓማኒ የሚባሉ ማብራሪያውችን ማገላበጥ፣ ታሪካዊ፣ ስዋሰዋዊ እና ቁማዊን ትርጉም ምን እንደሆነ ከሥሩ ማጥናት እጅጉን ያስፈልጋል።  ማጠቃለያ በመጨረሻም አንድ ሰው ለምን ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር መተዋወቁ ለሕይወቱ ምን ይጠቅመዋል? ያለ እንደሆነ አንደኛ፦ ኢየሱስ አምላኩና ጌታው እንደሆነ እንደሞተ እና በሦስተኛው ቀን ከሙታን እንደተነሳ ያምናል። ሁለተኛ፦ ክርስቶስ በከፈለው የቤዛነት ሥራ በኩል ብቻ የዘላለም ሕይወት አለህ ስለሚለው ነው። ሦስተኛ ፦ ሰው በሕግ ሥራ ፈጽሞ ሊጸድቅ ስለማይችል፣ በዚህም የተከፈለለትን የእዳ ክፍያ በክርስቶስ አምኖ ተስፋውንም በአለቱ ላይ ስለሚተክል ነው።(ሐዋ 4፥12) ስለዚህ አሁን ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር ያልተዋወቃችሁ ወገኖች ይህንን ታላቅ መጽሐፍ አግኝታችሁ ታነቡት ዘንድ እናበረታታችኋለን። በቃሉ ውስጥ የተገለጠውን እግዚአብሔርን ፊት ለፊት የምናይበት ሕያው መስታወት ቅዱስ ቃሉ ብቻ በመሆኑ በውጤቱ ክርስቶስ ኢየሱስን በማመን የሚገኘውን የዘላለምን ሕይወት እንደምታገኙ ባለ ሙሉ ተስፋዎች ነን፡፡

ኑ መጽሐፍ ቅዱስን እንተዋወቀው Read More »

የማርቆስ እና እስረኛው ታሪክ

በሰሞኑን በተነሳው በቻርሊ ከርክ ሕልፈት ምክንያት ሁለት ጽንፍ ጎራዎችን እንመለከታለን። አንዱ ጎራ በዚህ ሀሳቡ አልስማማውም ሲል ይኼኛው አይደለም እንዲያማ አይባልም በዚህ ሀሳቡ እጋራዋለሁ በማለት ሲወያዩ ስመለከት ነበር። በእርግጥ ቻርሊን በአንዳንድ ሀሳቦቹ ባልስማማም ነገር ግን በወጣቱ ዘንድ ያለውን ተጽዕኖ እና ወደ ኋላ ገሸሽ በማይለው አቋሙ ሁሌ የማደንቀው ሰው ነው። በሳልና አዕምሮውን የሚጠቀም፣ በልቡን የማያምንበት ከሆነ የማያደርግ ነበር። በኋላ በተለያዩ ገጾች የሚጻፉትንና ደጋግመው የሚመጡትን የተለያዩ ጽሑፎችና የምስል ቪዲዮዎችን ለመመልከት ሞክሬ ነበር። በእርሱም ህልፈት ምክንያት ብዙዎች ከኢ-አማንያን ወደ ክርስትና እንደመጡና ቤተክርስቲያንን ሥፍራ አጣን እስከማለት ደርሰው እንደተገኙ እንመለከታለን። ይኼንን ታሪክ ስመለከት በሞቱ ብዙዎችን መጥራቱን ሳስብ የማርቆስና የእስረኛው ታሪክ ጋር ከዚህ ቀደም ፊልጵስዩስን በማጠናበት ጊዜ ከጻፍኩት ጽሑፍ ጋር የቻርሊ ከርክ ታሪክ ተመሳሰለብኝ። የማርቆስ እና የእስረኛው ታሪክ በፊልጵስዩስ 1፥21 ላይ የተመሠረተ አፈ-ታሪክ ነው። ከታሪኩ በፊት ቃሉ እንዲህ ይነበባል፦ “ለእኔ ሕይወት ክርስቶስ፥ ሞትም ጥቅም ነውና።”  — ፊልጵስዩስ 1፥21 ማርቆስ በፊልጵስዩስ የሚኖር ወጣት ለእምነቱ ታጋይ ሰው ነበር። ማርቆስ በክርስትና ምክንያት ዘወትር በሮማውያን እና በቅርብ ወዳጆቹ መገለል ከዛም ታልፎ መከራ በገጠመው ቁጥር ኹል ጊዜ ወደ እስር ቤት ይሄዳል። በዛም እስር ቤት በእምነቱ ጽኑ የሚባለውን ጳውሎስን እንዲጎበኝ ይሄድ ነበር። የእስር ቤቱ ጨለማ ክፍል ሁልጊዜ ለማርቆስ አስጨናቂው መንገዱ ነበር፣ ነገር ግን ጳውሎስ በዚያ ውስጥ ሁልጊዜ ደስታ የተሞላበት ዓይን ነበረው። አንድ ምሽት ላይ እንደተለመደው ለጉብኝት በሚሄድበት ጊዜ ማርቆስ ስለ ጳውሎስ ከሚደርስበት መከራ መደሰት ምክንያቱ ምን እንደሆነ እንዲህ ሲል ጠየቀው፦ «ጳውሎስ፣ ነገ ሊገደሉህ ሲሆን እንዴት እንደዚህ ፊትህ ላይ ደስታ ይታያል? ሞትን አትፍራም?» ይለዋል ጳውሎስም ከትከሻው ላይ እጁን አሳረፈ እና እንዲህ አለ፦ «ማርቆስ፣ ከክርስቶስ ውጪ በዚህ ዓለም ሳለህ ጥሩ ሆነ መጥፎ የሚባል ነገር የለም። ለእኔ ሕይወት ክርስቶስ፥ ሞትም ጥቅም ነውና። ባለሁበት ዘመን ሁሉ ክርስቶስን እናገራለሁ፤ በዚህም የክርስቶስ አካል ፍጹማን ይሆኑ ዘንድ በመከራዬ ሁሉ አጽናናለሁ። በዚህስ ብሞት ግን፣ ከእርሱ ጋር እኖራለሁ። እኔ እንዴት እጎዳለሁ?» በማለት መለሰለት። ማርቆስ ተደነቀ። «እንግዲህ… በኑሮህም በሞትም ክርስቶስ ድሌ ነው የምትለኝ?» አለ። ጳውሎስም፦ «አዎን። ይህች ዓለምን እንዳልመስል በደማስቆ መንገድ ላይ ሕይወትና አገልግሎትን ሰጥቶኛል። በዛም በተቀበልኩት ሕይወት ሞት ወደ እኔ ቢመጣ አልሰጋም ምክንያቱም የምቀምሰው ጽዋ ክርስቶስን ራሱን ይሰጠኛል። ስለዚህ አንዳችም አልሰጋም።» በማለት መለሰለት። እነዚህ ቃላት በእሥረኛ ጠያቂው በማርቆስ ልብ ውስጥ በጽኑ ጠነከሩ። ከብዙ ዓመታት በኋላ፣ በፊልጵስዩስ ላይ ስደትና መከራ በክርስቲያኖች ላይ መጣ። በዛም መከራ ውስጥ ማርቆስ የጳውሎስን ቃል በልቡ አሰበ። በዚያም ሸንጎ ተይዞ ስለ እምነቱ ሞት ቅጣትን በማርቆስ ላይ ሊያደርሱበት በተሰለፉ ጊዜ፣ ቆመና እንዲህ ብሎ ቃሉን ተናገረ፦ «በህይወት መኖሬ በክርስቶስ ውስጥ አገልግሎት እና ፍሬያማ ሥራዬ ነው። ሞት ቢመጣ ደግሞ ከክርስቶስ ጋር መኖርን የሚሰጠኝ ሕያው ድልድይ ነው። ለእኔም ይህ ደግሞ የተሻለ ነው አላቸው።…» አጠገቡ የነበሩት፣ ሊገድሉት ከሚፈልጉት መካከልም አንዳንዶች የማርቆስን እምነት ምንኛ ነው? በማለት እርስ በእርሳቸው አንጎራጎሩ። ዳግመኛም ማርቆስ የመጨረሻ የክህደት ቃልህን አስፍርና ተናገር ባሉት ጊዜ « ለእኔ ሕይወት ክርስቶስ፥ ሞትም ጥቅም ነውና…» በማለት አጠናቀቀ ንግግሩን። የማርቆስም ሞት በፊልጵስዩስ ቤተክርስቲያንም በዙሪያዋ ባሉት ሁሉ ላይ ብዙዎች ጋር ደረሰ። ብዙዎች በጽናት ተመሰረቱ፣ በዛችም ከተማ ወንጌሉ ብዙዎችን እየለወጠ ሄደ። ይሄን እምነት መርሕ አድርገው የቤተክርስቲያን አባቶች ብዙዎች እንደ ሻማ ቀልጠውበታል። ለዚህም ነው ጠርጡልያንም ሲናገር The blood of the Martyrs is the seed of the Church(የሰማዕታት ደም የቤተክርስቲያን ዘር ነው) ያለው። በአጭሩ የቻርሊ ከርክ ፖለቲካ አቋም ምንድነው? የሚል ትርጉም ሳይሆን ጽሑፉ ትኩረት የሚሰጠው በእርሱ ህልፈት ምክንያት የመጣውን ሰዎች ባሰብን ቁጥር እግዚአብሔር በቃሉ ሞትም ጥቅማችን እንደሆነ የሚነግረን። በዚህ ዘመንስ እንደ እንቁ የምናያቸውን ምሑራንን ለማጥፋት ብዙዎች የሚያቅዱት። በዚህ ሁሉ ግን እግዚአብሔር ጽኑ እምነት ሰጥቷቸው የክርስቶስን ወንጌል ለማገልገል የተሰጡ ስንቶች ይሆኑ? እንጃ፤ ለእኛ ግን እግዚአብሔር በዚህ ጽኑ እምነት ይባርከንም።

የማርቆስ እና እስረኛው ታሪክ Read More »

የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነት

ክፍል 1 “እርሱ በባሕርዩ አምላክ ሆኖ ሳለ፣ ከእግዚአብሔር ጋር መተካከልን ሊለቀው እንደማይገባ አድርጎ አልቈጠረውም፤”  — ፊልጵስዩስ 2፥6 (አዲሱ መ.ት) አንድ አካል አምላክ ነው የሚባለው ወይም እንደ አምላክ ሊመለክ የሚገባው አምላክ ነኝ ብሎ ስለተናገረ ብቻ ወይም ብዙዎች አምላክነቱን ስላወጁለት አይደለም። በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ አምላክ ነኝ ብለው የተነሱ ነገሥታትን እንመለከታለን። ለምሳሌ፦ የጢሮስ ንጉስ እኔ አምላክ ነኝ ማለቱን(ሕዝቅኤል 28፥2-9) ስንመለከት ይህ ንጉሥ እኔ አምላክ ነኝ ስላወጀ ብቻ አምላክ ነው ብሎ መፈረጅ ፈጽሞ አይቻልም። በሰውም አጀብ አንድ አካል አምላክ ስለተባለም አምላክ ሊሆን አይችልም። ምክንያቱም የግሪክ ጣዖታት እንዲሁ ተብለው ምንነታዊ ለውጥ ስላላሳዩን። ክርስቶስ ኢየሱስ አምላክ ለመሆኑ የአምላክነት ግብሩን፤ ባህሪዎቱንና ሐልዎቱን በተለያየ መንገድ መጽሐፍ ቅዱስ ሲናገር፤ ኑባሬውን ሲተርክና ሲገልጽልን እንመለከተዋለን። ከእነዚህም የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ውስጥ አንደኛው የፊልጵስዩስ መልእክት ም2 ቁ6-7 ነው፦ ⁶ እርሱ በባሕርዩ አምላክ ሆኖ ሳለ፣ ከእግዚአብሔር ጋር መተካከልን ሊለቀው እንደማይገባ አድርጎ አልቈጠረውም፤ ⁷ ነገር ግን የባሪያን መልክ ይዞ፣ በሰውም አምሳል ተገኝቶ፣ ራሱን ባዶ አደረገ” ፊልጵስዩስ 2 (አዲሱ መ.ት) ὃς ἐν μορφῇ θεοῦ ὑπάρχων οὐχ ἁρπαγμὸν ἡγήσατο τὸ εἶναι ἴσα θεῷ, Προς Φιλιππησιους 2:6 በጽርዑ ሞርፌ/μορφῇ የሚለው ቃል ኑባሬያዊ መገኘትን፣ ሁናቴን ወይም ባህሪዎተ መልክን የሚገልጽ ቃል ሲሆን ክርስቶስ ኢየሱስ (ወልድ) እም ቅድመ አለም በኑባሬው በባህሪዎተ መልኩ ራሱ አምላክ ሆኖ የሚኖር አካል እንደሆነ ይገልጻል። በተጨማሪም በባለቤትነት ሙያ (Nominative case) የመጣው ሁፓርኾን/ὑπάρχων የሚለው ቃል በአሁን ጊዜ አመልካች ግስ(Present participle tense) መምጣቱ ወልድ ከዘላለም ጀምሮ ከአብ ጋር አብሮ ህያው አብሮ እኩል አብሮ ዘላለማዊ እንደሆነ በሚገልጽ መልኩ እንደመጣ የክፍሉን ሰዋሰው ይነግረናል። ይህም ደግሞ ለወልድ ኑባሬ ጅማሮ አለው ፍጡር እንጂ ፈጣሪ አይደለም ለሚሉት አርዮሳውያን እና ኢብዮናውያን (Ebionite/Ἐβιωναῖοι) በተለምዶው አዶፕሽኒስቶች የሚባሉት የምን*ፍቅና የአስተምህሮቶችን መሰረታቸውን የሚንድ ክፍል ነው። ሙግታችንን ጠበቅ ለማድረግ ያክል ከተመለከትን ደግሞ ወልድ አምላካዊ ባህሪ ከጥንተ ዘላለም ጀምሮ በዚሁ መልክ ሲኖር የነበረው አምላክ ወደ ፈጠራት ጠባበ አለም የሰውን ወይም የባሪያን ባህሪ(መልክ) ይዞ መምጣቱ “ከእግዚአብሔር አብ ጋር መተካከልን ሊለቀው እንደማይገባ አድርጎ አልቈጠረውም” በማለት ብርሃነ አለም ቅዱስ ጳውሎስ ፍንትው አድርጎ የወልድን መለኮታዊ ባህሪዎት ከእግዚአብሔር አብ ጋር እኩል እንደሆነ ያሳየናል። ከአምላክ ጋር እኩል መሆን ወይም በጽርዑ ቶ ኢናይ ኢሳ ቴኦ/τὸ εἶναι ἴσα θεῷ የሚለው ሐረግ እግዚአብሔር ወልድ ከእግዚአብሔር አብ ጋር በባህሪው እኩል ወይም አንድ አይነት ሆሙስዮስ/ὁμοούσιος እንደሆነ በግልጽ ሁኔታ ሲነግረን የአርዮሳውያንን መርሆተ ቃል የሆነውን ተመሳሳይ ወይም ተቀራራቢ ባህሪዎት ሆሞዮስዮስ/ὁμοιούσιος የሚለውን ምንፍቅና አፈር ከመሬት የሚደባልቅ ክፍል እንደሆነ እንመለከታለን። በቁጥር ሰባትን አንድ በአንድ ስንመለከተው “የባሪያን መልክ ይዞ” የሚለው ሐረግ በፊት የተገለጠበት ቅድመ ኑባሬያዊ ባህሪዎት እንደነበረው ቁልጭ አድርጎ ያሳየናል፤ እርሱም በቁጥር 6 ላይ እንዳየነው የወልድ አምላካዊ መልክ (ባህሪ) ከጥንተ ዘላለም ጀምሮ ገንዘቡ የሆነ ምንነት ነው። “በሰውም ምሳሌ ሆኖ” የሚለው አገላለጽ ደሞ ወደ ምድር በመጣ ጊዜ ፈጣሪ በፍጡራን ምሳሌ ሆኖ ሰዋዊ ባህሪዎትን እንደተላበሰ ያሳየናል። ቀጥሎም “ራሱን ባዶ አደረገ” የሚለው ደሞ አንድ ነገር ባዶ ሆነ የሚባለው ያ ነገር መጀመሪያውኑ የሆነ ነገር ሲኖረው ነው። ክርስቶስ ኢየሱስ ደግሞ ራሱን ባዶ አደረገ ሲባል አምላካዊ ሙሉነት የነበረው አካል ወደ ፈጠረው፣ ወዳዘጋጀው፣ ሰዋዊ ባህሪዎት ዝቅ ብሎ በመምጣቱ ነው። ስለዚህ ክርስቶስ ኢየሱስ ሰው ሁኖ ከመምጣቱ በፊት በአምላካዊ ሙሉነት የሚኖር አምጻኤ ኩሉ አምላክ እንደሆነ እንመለከታለን። በመጨረሻም የክርስቶስን አምላክነት የማያምኑ እንዲህ ሲሉ፦”…ክርስቶስ ኢየሱስ (ወልድ) በእግዚአብሔር ወይም በአምላክ መልክ መኖሩ አዳም በእግዚአብሔር መአልክና ምሳሌ በተፈጠረበት ሒሳብና ቀመር ነው…” ይሞግታሉ። ነገር ግን የሁለቱን ክፍሎች የጽርዑን የቃላት አገባብ እና አውዳዊ ምልከታ ባደረግን ጊዜ ፈጽመው የየቅል ሐሳብ እንደሆነ እንረዳለን፦ እግዚአብሔርም አለ፦ ሰውን በመልካችን እንደ ምሳሌአችን እንፍጠር/καὶ εἶπεν ὁ θεός Ποιήσωμεν ἄνθρωπον κατ᾽ εἰκόνα ἡμετέραν καὶ καθ᾽ ὁμοίωσιν…>>  — ዘፍጥረት 1፥26 በዘፍጥረት 1፥26 መልክ ብሎ የገባው የግሪኩ ቃል ኤይኮና/εἰκόνα ሲሆን ምሳሌ የሚለው ደሞ ሆሞዮሲን/ὁμοίωσιν በሚለው የቃላት አገባብ እንደተሰደረ እንመለከታለን። ኤይኮና/εἰκόνα የሚለው ቃል ኤይኮን/εἰκών ማለትም ምስለ መልክን መመሳሰል ወይም መቀራረብ(በውጫዊ ማንነት መገለጫ) የሚል ትርጉም አለው። እግዚአብሔር አምላክ ሰውን በእኛ መልክ(ኤይኮና ሄሜቴራን/εἰκόνα ἡμετέραν) እንፍጠር ሲል በጽድቅና ቅድስና(ኤር 4:24)፤ እንዲሁም በመገንዘብ ችሎታንና እውቀትን(ቆላ 3:10) የመሳሰሉትን የምስስሎሽ መገለጫዎች በሚገልጽ አገባብና አግባብ መምጣቱ ቅብል ነው። ነገር ግን የሰው ልጅ በእግዚአብሔር መልክና አምሳል መፈጠሩ በእርግጥ የሚካፈለው ባህሪ እንዳለው ሁሉ የማይካፈለው ባህሪ አለ። በዛው በፊልጵስዩስ መልእክት 1:7 እና 2ኛ ጴጥሮስ 1፥4 ላይ የእግዚአብሔር የባህሪው ተካፋዮች እንደሆንን ይናገራል፦ “ስለ ክፉ ምኞት በዓለም ካለው ጥፋት አምልጣችሁ ከመለኮት ባሕርይ ተካፋዮች(κοινωνοὶ φύσεως) በተስፋ ቃል እንድትሆኑ፥ በእነዚያ ክብርና በጎነት የተከበረና እጅግ ታላቅ የሆነ ተስፋን ሰጠን።”2ኛ ጴጥሮስ 1፥4 ተካፋይ ወይም በግሪኩ ኮይኖኖስ/κοινωνός የሚለው ቃል የሰው ልጅ ከእግዚአብሔር ፈጽሞ የማይካፈለው ወይም የቀረበት ነገር እንዳለ አመላካች ነው። ይህንን ሐሳብ በሌላ ክፍል በስፋት እንመለከተዋለን። ነገር ግን ክርስቶስ ኢየሱስ ከእግዚአብሔር አብ ጋር የማይጋራው ሆነ የማይካፈለው ባህሪ የለም። ከላይ በፊልጵስዩስ መልእክት 2:6 ከአብ ጋር በመለኮተ ባህሪዎት እኩል ወይም አንድ እንደሆነ ተመልክተናል። ስለዚህ አምላክ ክርስቶስ ኢየሱስ በአምሳለ ሰውነት መገለጡ (እንደ ሰው መብላት መጠጣቱ፤ መተኛት መነሳቱ፤ መወለድ ማደጉ ወዘተ) መለኮታዊ ክብር እንደሌለው የሚያሳየን ተግባር አይደለም። እርሱ ወደዚች ወደ ፈጠራት አለምና ሰውነት ከመገለጡ በፊት አምላካዊ ምንነት፤ ክብርና መለኮታዊ ኑባሬ ከጥንተ ዘላለም ጀምሮ ገንዘቡ ያደረገ ኃያል አምላክ ነው።

የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነት Read More »

ንጉሥ ሄነሪ ስምንተኛ እና የአንግሊካን ቤተክርስቲያን?

ክፍል አንድ አብዛኛውን ጊዜ በአንግሊካን ቤተ ክርስቲያን ላይ ከሚነሱ ትችቶች መካከል ትልቁን ሥፍራ የሚይዘው የንጉሥ ሄነሪ ስምንተኛ(Henry VIII) ትዳር መፍረስ ምክንያት የእንግሊዝ ቤተክርስቲያን በዛ መንሥኤ የተጀመረች አድርጎ መሞገት ነው። ይሄ ደሞ የቤተ ክርስቲያንቱን ታሪክና አስተምህሮን በአግባቡ ካለማወቅ የሚነሳ ትችት ተደርጎ በብዙ ምሑራን ዘንድ የሚወሰድ ነው። ከክርስትና ውጭ ያሉ ሃይማኖታዊ ድርጅቶች(ሙስሊሞች፣ አርዮሳውያን፣ ሰባልዮሳውያን…) ክርስትና የጀመረው በንጉሥ ቆሰንጠንጢኖስ ነው ከሚል የአፈ ታሪክ የማይለይ ሙግትና በብዙ የተወሳሰበውን የታሪክ፣ የፖለቲካ እና የሥነ መለኮት እይታን ለማቅለል የሚሞከር ከንቱ ትግል ነው በማለት መግለጽ ይቻላል። በዚህ ጽሑፍ ደግሞ ከመጀመሪያው የንጉሥ ሄነሪ ስምንተኛ እና የንግሥት ካትሪን ትዳር ለመመልከት እንሞክራለን። የንጉሥ ሄነሪ ስምንተኛ ታላቅ ወንድም የነበረው አርተር በ1501 ካትሪንን አገባ። አምስት ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ በሕመም ምክንያት ይሞታል። ያገባትም የ16 ዓመቷ ልጃገረድ ንግሥት ካትሪን ባልቴት ትሆናለች። የንግሥት ካትሪንንና የልዑል አርተር ጋብቻ በስፔንና እና በእንግሊዝ መሃል ጥሩ የሆነ ፖለቲካዊ ግንኙነት ፈጥሮ ነበር። ንጉሥ ሄነሪ ስምንተኛም ይህን ፖለቲካዊ ግንኙነት እንዲቀር ስላልፈለገ ካትሪንን ያገባታል። እንደ ብዙዎች ምልከታ መሠረት ዘንድ ይህ ትዳር የተሳካ አልነበረም ይባላል። ወቅቱም የህፃናት ሞት ከፍተኛ  የነበረበት ጊዜ ስለነበር ከወለዳቸው ሦስት ወንዶችና ሶስት ሴቶች ልጆች መሀል 1 ልዕልት ማርያም (Mary I “Bloody Mary”) ነበር የተረፈችው።(ስለ Mary በክፍል ሁለት በስፋት እንመለከታለን።) በዚህ ትዳር ውስጥ የሚተካውን ወንድ ልጅ በማጣቱ በትዳሩ ላይ ጥያቄ ማንሳት ጀመረ። ለዚህም ይሆነው ዘንድ በኦሪት ዘሌዋውያን 20:21፦ “ ‘ማንኛውም ሰው የወንድሙን ሚስት ቢያገባ አድራጎቱ ርኩሰት ነው፤ ወንድሙን አዋርዷልና፣ ያለ ልጅም ይቀራሉ። በሚለው ቃል ላይ በመመስረት የወንድሙን ሚስት በማግባቱ እንደተረገመና ትክክለኛ ጋብቻ እንዳልሆነ በ1527 ዓ.ም ለሮማን ካቶሊክ ቤተክርስቲያን እና ለፖፕ ቀለሜንጦስ ሁለተኛ በጥያቄ መልክ ማቅረብ ጀመረ። እዚህ ታሪክ ላይ ልብ ልንለው የሚገባን ነገር ቢኖር በአንግሊካን ቤተክርስቲያን ሆነ በሮማን ካቶሊክ ፍቺ እንደማይፈቀድ ነው። ነገር ግን የንጉሡ ሄነሪ ስምንተኛ ጥያቄ የፍቺ ጥያቄ ብቻ አልነበረም ጋብቻው መጀመርያውኑ ትክክለኛ ጋብቻ ነው ወይ የሚል ነው ።(annulment ‘a legal procedure within secular and religious legal systems for declaring a marriage null and void’) በዚህም የጋብቻውን ትክክለኛነት ጠይቆ ትክክለኛ አለመሆኑ በሮማን ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያኗ ህግ ከተረጋገጠ ጋብቻው መጀመሪያውኑ ትክክለኛ አይደለም ተብሎ ሊወሰንለት ይችላል። ለዚህም በተለያዩ ጊዜያቶች በሮማን ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ይህ ስርዐት ሲተገበር ታይቷል። ለምሳሌ ታዋቂው አሜሪካዊው ፖለቲከኛ ቴድ ኬኔዲ(Ted Kennedy) በጋብቻው ወቅት ታማኝ አለመሆኑን አምኖ የሃያ አራት ዓመት ጋብቻውን በሮማን ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ፊት ትክክለኛ ጋብቻ እንዳልነበር ተቆጥሮለት ተለያይተዋል። ሌላኛው ደግሞ ዮሴፍ ኬኔዲ  ሁለተኛ(Joseph Kennedy II, 2007 እ.ኤ.አ) እና ታዋቂው ፈረንሳያዊው ገዥ ናፖሊዮ ቦናፓርቲ እና የንጉሥ ኤድዊግ(Eadwig 959 እ.ኤ.አ አካባቢ) ለዚህ ታሪክ ተጠቃሽ ናቸው። ነገሩን ለየት የሚያደርገው ደግሞ በዚህ ዘመን እንደሚታወቀው አይነት ፍቺ በመካከለኛው ዘመን በነበሩት ሰዎች ዘንድ አልነበረም። የጋብቻን ትክክለኛነት ማረጋገጥ እና በመጀመሪያውኑ ጋብቻ እንዳልነበር ማስመስከር (Annulment / Declaration of Nullity) የተለመደ ነበር። በዚህም ዘመንም የሮማን ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን በህግዋ ውስጥ ይህ ጋብቻ ነው ለመባል ማሟላት ያለበትን ነገሮች በዝርዝር ተቀምጧል።(the code of canon of law 1095-1107) ለምሳሌ ያህል ሁለቱም ተገቢዎች በፈቃዳቸው መሆን አለበት ቤተሰብ(የደም ዝምድና) ያላቸው መሆን የለባቸውም። ማንኛውም ክህነት የተቀበለ መሆን የለበትም (ቄስ ,ጳጳስ)  የመሳሰሉትን ህጎች የያዘ ነው። ስለዚህ የንጉሥ ሄነሪ ስምንተኛ ጥያቄም ከዚህ የተለየ አልነበረም። ለጋብቻው ትክክለኛ አለመሆን እንደ ምክንያት አድርጎ ያስቀመጠው ነገር፦ የወንድሙን ሚስት ማግባት ትክክለኛ ጋብቻ አይደለም በመፅሐፍ ቅዱስ ህግ ጋር ይጋጫል። የወንድሙን ሚስት በፖፕ ጁሊየስ ሁለተኛ ፈቃድ(papal Dispensation) ማግባቱ ትክክል አይደለም። ንግሥናውን የሚተካ ወንድ ልጅ አለማግኘቱን እንደ እርግማን ይቆጥረው ነበር። እነዚህን እንደ ምክንያት አድርጎ በማቅረብ ለፖፕ ቀለሜንጦስ ሁለተኛ ጥያቄውን አቀረበ ነገር ግን የጠበቀው መልስ በተቃራኒ ሆኖ ይህን ሊፈቅድለት አልወደደም። ምክንያቶቹም ተብለው የሚነሱት፦ አንደኛ፦ የንጉሥ ሄነሪ ሚስት ካትሪን በጊዜ ኃያል የሚባለው የሮማን ገዢ የሆነው የስፔን ንጉሥ የቻርለስ አምስተኛ አክስት(Holy roman Empire) ስለ ነበረች ነበር።ንጉሥ ሄነሪ ጥያቄውን ባቀረበበት በ1527 በዛው ዓመት በቁጥር ከሃያ ሺ የሚበዙ ደሞዝ ያልተከፈላቸው ወታደሮች(አስራ አራት ሺህ የሚሆኑ ጀርመናዊ ሉተራውያን ወታደሮች እና ስድስት ሺህ ስፔናውያን እና ጣሊያንናዊ ወታደሮች) ንቅናቄ የሮማን አገዛዝና ያደከመ፣ ከሃምሳ አምስት ሺህ ወደ አስር ሺህ የሮም ህዝቡ ቁጥር የቀነሰበት፣ እስከ ሁለት መቶ የሚሆኑት ወታደሮች ፖፑን ለመጠበቅ የሞቱበት፣ ፖፑም በአማፅያኑ እጅ ገብቶ በእስር የነበረበት ጊዜና መንበረ ጴጥሮስ በትልቅ ሀዘን ውስጥ የሆነበትም ጊዜ ነበር። ከዚህም ክስተት(the sack of Rome 1527) ዘጠኝ ወር ያህል ፖፑ ታግተው ከቆዩ በኃላም ከገበሬዎች ጋር በመመሳሰል ያመለጡበት ጊዜ ነበር። በዚህ መሐልም ግን የንጉሥ ሄነሪ የጋብቻ ጥያቄ አልተመለሰም ነበር። ጋብቻውን ትክክለኛ አይደለም ቢሉ በዚያን ጊዜ የሮማን ንጉሥ የነበረው ቻርለስ አምስተኛ ስለሚያስተዳድሩአቸው ከእርሱ ጋር ያላቸውን ግንኙነት ስለሚያሻክር ፈርተውም ነበር። ሁለተኛው፦ ምክንያት ንጉሥ ሄነሪና ካትሪንን ያጋባው የቀድሞ ፖፕ ጁሊየን ሁለተኛ ስለነበር የእሱን ስልጣን መቃወም ስላልነበረበት ነበር። ሦስተኛው፦ ምክንያት ደግሞ ካትሪን ከአርተር (ከንጉሥ ሄነሪ ወንድም) ጋር በጫጉላ ወቅት ስጋዊ ተራክቦ አልነበረንም ማለቷ ነው። ጋብቻ የሚፈፀመው በስጋዊ ተራክቦ ነው ተብሎ ስለሚታመንም ካትሪን የመጀመሪያ ጋብቻዋ ወቅት ስጋዊ ተራክቦ ካልነበር ከንጉሥ ሄነሪ ያላት ጋብቻ ትክክለኛ ይሆናል። ሆኖም እርሱዋ ይህንን ብትልም የልዑል አርተር የቅርብ ጓደኞች ግን ከእርሷ በተቃራኒ ቆመው ነበር የተናገሩት። በዚህ ምክንያት ለንጉሥ ሄነሪ አለመፈቀዱ ንጉሡን አስቆጥቶታል። ስለዚህም በ1534 ዓ.ም እራሱን በእንግሊዝ ቤተ ክርስቲያን ዋና የቤተ ክርስቲያን የበላይ ሃላፊ አድርጎ በመሾም ከፖፕ ቀለሜንጦስ ሁለተኛ ቤተ ክርስቲያኒቱን ለያት። ንጉሡ ራሱን የቤተክርስቲያን የበላይ አድርጎ በሾመበት ወቅት ብዙ ቢሾፖች ዲያቆናቶች እና መነኩሴ በመቃወማቸው ምክንያት በእምነታቸው ሰማዕታት ሆነዋል። በ1538 ዓ.ም ፖፕ ጳውሎስ ሶስተኛ ከሮማን ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን አወገዘው(excommunicate) ተደረገ። ከዚያም በዚህ ሁኔታ ውስጥ እያለ ከአርክ ቢሾፕ ቶማስ ክራመር ጋር በመሆን ደግሞ ጋብቻ ትክክለኛ እንዳልሆነ አጸደቀ። ግን ብዙም ሳይቆይ ደግሞ በ1533 አናን አገባ። የሄነሪ ጋብቻ ታሪክ በዚህ አያበቃም እስከ ዘመኑ መጨረሻ ድረስ ስድስት ሚስቶች በተለያዩ ምክንያቶች ነበሩት። ቢሆንም ዘሩን የሚተካ ልጅ ከኤድዋርድ ውጭ አላገኘም ነበር። ኤድዋርድን ቢተካውም ስድስት አመት ከገዛ በኋላ በ15 ዓመቱ በህመም ሞቷል። በዚህ ሁሉ ታሪክ በስተ መጨረሻም ግን ልንረዳው የሚገባው የእንግሊዝ ቤተ ክርስቲያን በንጉሥ ሄነሪ ጊዜ ፕሮቴስታንት እንዳልነበረችና ሄነሪ ካቶሊክ እንደ ነበር። ሉተርንም የሚቃወም ጽሑፍ “ሰባቱ ቅዱስ ምስጥራት መከላከያ”(Defense of the Seven Sacraments/Assertio Septem Sacramentorum) በማለት ጽፎ የነበር መሆኑን ማወቅ አለብን። በዚያም ከፖፕ ሊዮ ኤክስ በ1521 ዓ.ም “የእምነት ጠባቂ”(“Defender of the Faith”) የሚል ስም ተሰጥቶት ነበር። በዚህም ካቶሊክ ሆኖ ነበርም የሞተው። በንጉሥ ሄነሪ ጊዜ በአንግሊካን ቤተ ክርስቲያን ንግሡ መጥቶ የአስተምህሮ ለውጥ በምንም አይነት መልኩ አላደረገም ነበር። ስለዚህ አንግሊካን ቤተ ክርሰቲያን በንጉሡ ተመሥርታለች የሚለው አስተምህሮ በዚህ ውድቅ ይሆናል። ነገር ግን የአንግሊካን ቤተክርስቲያን በ597 ዓ.ም በፖፕ ጎርጎርዮስ አማካኝነት የካቲቤሪውን ቅዱስ አውግስጢኖስ ወደ እንግሊዝ በመላክ ወደ ሮም ቤተክርስቲያን ውስጥ ተጠቅልላ ባካተተቻት ከአንድ ሺህ ዓመታት በኃላ ቤተክርስቲያኒቱ ከሮም ውጭ ሆነች። ንጉሥ ሄነሪ የእንግሊዝ ቤተ ክርስቲያንን ከሮማን ካቶሊክ እንደ ቀድሞዋ መለየቱ ለተሐድሶው የማይካድ ጥቅም ቢኖረውም ነገር ግን ያደረጋቸው ነገሮች እና ሕይወቱ ሙሉውን የአንግሊካን ቤተ ክርስቲያንን ታሪክ ለመግለጽ የማይችል መሆኑን መገንዘብ አለብን። ምክንያቱም የአንግሊካን ቤተ ክርስቲያንን ለመረዳት ከዚህም ያለፈ የተወሳሰበ የታሪክና የስነመለኮት ጥልቀት ውስጥ ዘልቆ መግባት አለብን። የአንግሊካን ቤተ ክርስቲያን መልክ ማቆጥቆጥ የተጀመረው በ1536 ዓም የአስር የሃይማኖት አንቀጾች (Ten Articles) (የካቶሊክ እምነት ያለው ትንሽ በተሃድሶ ሃሳብ ተጽዕኖ ያለበት) ከዚያም 1539 ዓም ስድስት የሃይማኖት አንቀጾች (six articles of faith) (አጥባቂ

ንጉሥ ሄነሪ ስምንተኛ እና የአንግሊካን ቤተክርስቲያን? Read More »

የኒቂያ ጉባኤ እና ጥንታዊያን አበው

ለሙስሊም ሰባክያን ሙግት ምላሽ ሰሞኑን በሙስሊሞች ዘንድ በማህበራዊ ሚዲያ ሲሰራጩ ከነበሩ ሙግቶች መካከል አንዱ ተከታዩ አንድ ሙስሊም የጻፈው ጽሑፍ ነው። የዚህ ጽሑፍ አዘጋጅ የዕውቀቱ ልክ በጽሑፎቹ ውስጥ የሚታየው ከሆነ ራሱን የማስተማር ብቃት እንዳለው ሰው በመቁጠር ለመጻፍ መድፈሩ፤ አንባቢያኑም ደግሞ ይህንን ሙግት ከቁም ነገር ቆጥረው መቀበላቸው የሚያሳዝን ነው። ሙግቱም እንዲህ ሲል ይጀምራል፦ አብዱል በአሏህ ስም እጅግ በጣም ሩኅሩህ እጅግ በጣም አዛኝ በሆነው፡፡ 112፥3 «አልወለደም አልተወለደምም»፡፡ ጥንት ላይ የነበሩ ነቢያት እንዲሁ ኢየሱስ እና ሐዋርያት አሓዳዊያን”Unitarian” የነበሩ ሲሆን ከሐዋርያት ኅልፈት በኃላ የተነሱ የቤተክርስቲያን አበው ደግሞ በሂደት “ክልዔታውያን”Binitarian” ነበሩ። ከክልዔታውያን አበው መካከል ጠርጡሊያኖስ”Tertullian” ስለ ወልድ ሲናገር እንዲህ ይለናል፦ “አብ አጠቃላይ ባሕርይ ነው፥ ነገር ግን ወልድ የአጠቃላዩ መገኘት እና ክፍል ነው” (Against Praxeas (Tertullian), Chapter 9) መልስ የብሉይ ኪዳንን ቅዱሳት መጽሐፍት ስንመለከት እግዚአብሔር አምላክ ነጠላ አንድ ነበረ ማለት አንችልም። ለዚህም ማሳያ መጽሐፍ ቅዱስ በዘፍጥረት 1፥26 እንዲህ ይላልና፦ “እግዚአብሔርም አለ፦ ሰውን በመልካችን እንደ ምሳሌአችን እንፍጠር፤ የባሕር ዓሦችንና የሰማይ ወፎችን፥ እንስሳትንና ምድርን ሁሉ፥ በምድር ላይ የሚንቀሳቀሱትንም ሁሉ ይግዙ።” የእግዚአብሔርን ሥሉስ አሓዳዊነት ከሚያመለክቱ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች መካከል አንዱ ከላይ ያነበብነው ጥቅስ ነው። እግዚአብሔር አብ ዓለማትን በልጁ መፍጠሩን (ዕብ1፥2፤ ዮሐ1፥3፤ ቆላ1፥16-17) እንዲሁም ደግሞ ፍጥረትን በማስገኘት ሒደት ውስጥ መንፈስ ቅዱስ ጉልሕ አስተዋጽኦ እንደነበረው ቅዱሳት መጻሕፍት አበክረው ይነግሩናል (ዘፍ 1፥3 ፤ ኢዮ33፥4)። በዘፍጥረት 1፥26 ላይም በብዙ ቁጥር ግስ “እንፍጠር” (נַעֲשֶׂה “ናዓሴህ”)፣ በብዙ ቁጥር ስሞች “በመልካችን” (בְּצַלְמֵ֖נוּ “ቤጻልሜኑ”) እንዲሁም “ምሳሌአችን” ( כִּדְמוּתֵנוּ ”ኪድሙቴኑ”) ማለቱ አሐዱ ሥሉስን እንደሚያመለክት በርካታ የመጽሐፍ ቅዱስ ምሑራን የሚስማሙበት እውነታ ነው፡፡ በዚህ ርዕሰ ጉዳይ ላይ በገጻችን የጻፍነው ጽሑፍ መመልከት ይቻላል።[1] ይህ ሙስሊም ጸሐፊ ቀጠል አድርጎ የቤተክርስቲያን አበው ሥላሴያውን አልነበሩም ብሎ በድፍረት ይናገራል። ነገር ግን ይህ ፍጹም ሐሰት እና ቅጥፈት ነው። ይባስ ብሎ ጠርጡሊያኖስንም ጨምሮ የጥንት ቤተክርስቲያን አባቶች “Binitarian” ናቸው ይለናል። በዚህ ንግግሩ ጸሐፊው የቤተክርስቲያን ታሪክ እውቀት የለውም ወይም ደግሞ ሆነ ብሎ አንባቢያኑን እየዋሸ ነው ማለት ነው። ሙስሊሙ ወገናችን ላነሳው ሀሳብ ምላሽ ከመስጠታችን በፊት በትምህርተ ሥላሴ ላይ የቤተ-ክርስቲያን አበው የነበራቸው አቋም ጥርት ያለ እንደነበር እስኪ በጥቂቱ እንመልከት፦ 1) ፖሊካርፕ (Polycarp):- በ70ዓ.ም ተወልዶ በ155 ዓ.ም ወይም በ160 ዓ.ም የሞተ፣ የሐዋሪያው ዮሐንስ ደቀ መዝሙር የነበረ ሲሆን የሰምርኔስ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ የነበረ ሰው ነው። ትምህርተ ሥላሴን በተመለከተ እንዲህ ይላል፦ ሁሉን ቻይ እግዚአብሔር ሆይ…ዘላለማዊና ሰማያዊ በሆነ ሊቀ ካህናት፣ በምትወደውና ባከበርኸው ልጅህ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ለአንተና ለእርሱም እንዲሁም ለመንፈስ ቅዱስ አሁንም ሆነ ለዘላለም ክብር ይሁን[2] 2) ዮስጢኖስ ሰማዕት(Justin Martyr) ፦ በቤተክርስቲያን የእምነት ተሟጋችና አቃቤ እምነት የነበረው ይህ አባት በ100 ዓ.ም ተወልዶ በ165 ዓ.ም እንደሞተ ይገመታል። ይህ አባት በአቅብተ እምነት ጽሑፉ ላይ ትምህርተ ሥላሴን በተመለከተ እንዲህ በማለት ጽፏል፦ የዓለማት ጌታ በሆነው በእግዚአብሔር አብ፣ በመድሐኒታችንም ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲሁም በመንፈስ ቅዱስ ስም በውሃ መታጠብን ያገኛሉ።[3] 3) አግናጢዮስ ዘአንጾኪያ(Ignatius of Antioch) ፦ የአንጾኪያ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ የነበረና ከ98 ዓ.ም እስከ 117 ዓ.ም መካከል ሰማዕት እንደሆነ የሚነገርለት አባት ክርስትናን ከመናፍቃን በመከላከሉ ዙሪያ ብዙ የጻፈ ዐቃቤ ክርስትና ነው። ትምህርተ ሥላሴን በተመለከተ እንዲህ በማለት ጽፏል፦ በጌታችንና በሐዋርያት ትምህርት እድትጸኑ፣ የምታደርጉት ነገር ሁሉ በስጋና በመንፈስ እንዲከናወንላችሁ፣ በእምነትና በፍቅር፤ በወልድ፣ በአብና በመንፈስ ቅዱስ፣ በመጀመሪያው እና በመጨረሻው፤ ከተወደደው ጳጳሳችሁ፣ በጎ ከሆነው የሽማግሌአችሁ መንፈሳዊ አክሊል፣  እናም እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ካሉ ዲያቆናት ጋር አጥኑ። በስጋችሁም በመንፈሳችሁም አንድነት እንዲኖራችሁ ክርስቶስ ኢየሱስ ለአብ በስጋው እንደተገዛለት፣ ሐዋርያት ለክርስቶስ ለአብ እና ለመንፈስ ቅዱስ እንደተገዙ፣ እናንተም ለጳጳሳችሁ እና እርስ በእርሳችሁ ተገዙ(ታዘዙ)። [4] 4) ጠርጡሊያኖስ ወይም ተርቱሊያን (Tertullian 160-215) አፍሪካዊ ዕቃቤ ክርስትና እንዲሁም የነገረ መለኮት ሊቅ ነው። የጥንቷ ቤተ ክርስቲያን አባት የሆነው ጠርጡሊያኖስ በሥላሴያዊ አስተምህሮ ላይ ለሚነሱ ኑፋቄዎች መልስ በመስጠትና በክርስቲያናዊ ሥነ-መለኮት ከሚሰሩ አቃብያነ አባቶች መካከል አንዱ ነው። ለምሳሌ በመናፍቃን ሙግት ላይ ባነሳው በፕራክሲየስ (against praxeas) የሞዳሊዝም አራማጅ የሆነው የፓትሪፓሺያን(Patripassian) ሐሳብ አንስቶ እንዲህ ሲል በሙግቱ ላይ ጽፏል፡- ሶስቱ አብ፣ ወልድና መንፈሱ ናቸው። ሶስት ናቸው። ነገር ግን በሁናቴ አይደለም በግብር እንጂ፤ በኑባሬም አይደለም በአካል እንጂ፤ በስልጣን ወይም በሐይል አይደለም በገጽታ እንጂ ሆኖም ግን እግዚአብሔር አምላክ አንድ ኑባሬ፣ ስልጣን፣ ሐይል አለው ምክንያቱም በአካል፣ በግብርና በአይነት በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ የተገለጠ አንድ አምላክ ነውና..[5] እንግዲህ ጠርጡሊያኖስ እና ሌሎች በርካታ አበው አብ፣ ወልድና መንፈስ ቅዱስ ከዘላለም ያለመሽቀዳደም እንዲሁም ያለመነጣጠል አሐዱ ሥሉስ እንደነበሩ ይነግሩናል። እንደ ሮሙ ቀለሜንጦስ(30-95)፣ ሔሬኒየስ (115-190) እና ቀጰዶቃውያን አበው (Cappadocian Fathers) ያሉ የቂሳርያው ትልቁ አባት ባስልዮስ፣ ጎርጎርዮስ ዘንዚናዙ፣ ጎርጎሪዮስ ዘኑሲስ እንዲሁም ሌሎች የቤተክርስቲያን አባቶች እንዘርዝር ብንል ትምህርተ ሥላሴን በተመለከተ በድርሳናቸው የጻፉትን እልፍ መረጃ እናገኛለን። ስለዚህ ሙስሊሙ ጸሐፊ “የቤተክርስቲያን አባቶች ስለ ሥላሴ ግንዛቤ የላቸውም ይልቅ አብና ወልድን ብቻ ጠቅሰው መንፈስ ቅዱስ ህልውና የለውም ብለዋል” በማለት “ክልዔታውያን “Binitarian” ነበሩ” በማለት በጽሑፉ ያሰፈረው ፈጽሞ ከእውነት የራቀ ነው። ይህን መሠል ሙግት ደሞ ከላይ ባስቀመጥናቸው የአባቶች ትምህርት ውድቅ ይሆናል። በመቀጠል ይህ ሙስሊም ጸሐፊ ሙግቴን ይደግፋል በማለት የአርዮሳውያንን ሙግት በመውሰድ ለመሞገት ሲጣደፍ ይስተዋላል። ሙስሊሙ ጸሐፊ ይህንን ሀሳቡን ለመደገፍ የጠቀሰው የጠርጡሊያኖስ ሥራ ከሆነው “Against Praxeas” ከተሰኘው ጽሁፍ ነው። ይህ አባት በጽሑፉም ሆነ በቃል የሥላሴን ትምህርት እውነተኝነት እየተሟገተ እና የሞዳሊዝምን (አብ፣ ወልድ እና መንፈስ አንድ ነጠላ አካል ነው ለሚሉ) ትምህርት አቀንቃኝ መናፍቃን እየሞገተ የጻፈው ጽሁፍ ነው። በዚህ ዐውደ-ጽሑፍ ጠርጡሊያኖስ የሚከራከረው በሦስት አካል ስለተገለጠው አንዱ መለኮት ነው። በምዕራፍ 9 ሙሉ አውዱ እንዲህ ሲል ይጽፋል፦ “Bear always in mind that this is the rule of faith which I profess; by it, I testify that the Father, and the Son, and the Spirit are inseparable from each other, and so will you know in what sense this is said. Now, observe, my assertion is that the Father is one, and the Son one, and the Spirit one, and that They are distinct from Each Other. This statement is taken in a wrong sense by every uneducated as well as every perversely disposed person, as if it predicated a diversity, in such a sense as to imply a separation among the Father, and the Son, and the Spirit.” “እኔ የምመሰክረው የእምነት መርህ ይህ መሆኑን ልብ በሉ። በዚህም አብ፣  ወልድና መንፈስም የማይነጣጠሉ እንደ ሆኑ እመሰክራለሁ። ነገር ግን በምን መንገድ ይህ እንደሚባል አስተውሉ።  እንግዲህ የኔ ሙግት “አብ አንድ እንደ ሆነ፣ ወልድም አንድ እንደሆነ፣ መንፈስም አንድ እንደ ሆነ፤ ነገር ግን እርስ በርሳቸውም ልዩ (distinct) እንደ ሆኑ ነው። ይሄም አገላለጽ ባልተማረ ሁሉ እንዲሁም ጠማማ አስተሳሰብ ባላቸው ሰዎች ሁሉ በተሳሳተ መንገድ ይወሰዳል። በአካላቱ[በአብ፣ በወልድ እና በመንፈስ] መካከል መለያየትን እንዳለብ በሚያመለክት መልኩ ብሎም በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ መካከል  መነጣጠል እንዳለ በማሳየት አጣምመው ይተረጉማሉ።[6] ሙስሊሙ ጸሐፊም ከላይ ጠቅሶ የጻፈው በዚህ ምዕራፍ ውስጥ የተጠቀሰ ሲሆን። ከአውዱ ውጭ ገንጥሎ በማውጣት ለአንባቢያኑ ጽፎላቸዋል። የጠርጡሊያኖስ ጽሁፍ እንዲህ ይነበባል፦ “Thus the Father is distinct from the Son, being greater than the Son, in as much as He who begets is one, and He who is begotten is another; He, too, who sends is one, and He who is sent is another; and He, again, who makes is one, and He through whom the thing is made is another……..Lord

የኒቂያ ጉባኤ እና ጥንታዊያን አበው Read More »

የባሕርዩ ምሳሌ?

በማህበራዊ ድህረገጽ ላይ ሲዘዋወሩ ከነበሩ ሙግቶች መካከል አንድ ጥያቄ ተቀምጦ ነበር። ይኼም ሙግት ኢየሱስ ፍጡር ነው ከሚል ከአንድ አርዮሳዊ በተለምዶ የይሖዋ ምሥክሮች ቤተ ጎራ የሚመደብ ነው። ኢየሱስ ፍጡር ነው ያለውም ከዚህ ጥቅስ የተነሳ ነበር ጥቅሱ እንዲህ ይነበባል፦ “እርሱም የክብሩ መንጸባረቅና የባሕርዩ ምሳሌ ሆኖ፥ ሁሉን በስልጣኑ ቃል እየደገፈ፥ ኃጢአታችንን በራሱ ካነጻ በኋላ በሰማያት በግርማው ቀኝ ተቀመጠ፤”  — ዕብራውያን 1፥3 ምሳሌ ሲባል ሰው በእግዚአብሔር ምሳሌ ተፈጥሯል እናም ኢየሱስ የእግዚአብሔር ምሳሌ ነው። ስለዚህ ፍጡር ነው የሚል ድምዳሜን አስቀምጦም ነበር። መልስ ምሳሌ የተባለበት ምክንያት ኢየሱስ በትክክል አብን የሚገልጥ መሆኑን ለማመልከት እንጂ ፍጡር መሆኑን ለማሳየት አይደለም፡፡ ኢየሱስ የእግዚአብሔር አብ ምሳሌ መኾኑ የተጠቀሰበት አምላክነቱን ለክርክር ሊቀርብ በማይችልበት ኹኔታ የሚገልጥ ሌላ ጥቅስ በዕብራውያን መልዕክት ውስጥ ይገኛል(ዕብራውያን 1፥2 ዕብራውያን 1፥8 እና ሌሎችም)። ከጠያቂያችን ጥቅስ ግን ተነስተን በአጭሩ መልስ እንስጥ፡- “እርሱም የክብሩ መንጸባረቅና የባሕርዩ ምሳሌ ሆኖ፥ ሁሉን በስልጣኑ ቃል እየደገፈ፥ ኃጢአታችንን በራሱ ካነጻ በኋላ በሰማያት በግርማው ቀኝ ተቀመጠ፤”  — ዕብራውያን 1፥3 “የባሕርዩ ምሳሌ” ተብሎ የተተረጎመው “ሁፖስታሴዎስ ካራክቴር” የሚል የግሪክ ሐረግ ሲሆን ካራክቴር የአንድን ነገር ትክክለኛ፣ ያልተሸራረፈ፣ ከዚያኛው አካል ያላነሰ፣ እኩል የሆነ ማንነት የሚያሳይ ነው፡፡ ይህ “ምሳሌ” ከዚያኛው አካል ጋር በኹሉም ረገድ ፍጹም ተመሳሳይ ነው ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ይህ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የሚነግረን ወልድ ከአብ ልዩ መኾኑን፤ ነገር ግን ደግሞ ከአብ ጋር ፍጹም እኩል መኾኑን ከምንም ዓይነት ጥርጣሬ በፀዳ ኹኔታ የሚገልጥ ክፍል ነው፡፡[1] ስለዚህ ይሄ ክፍል ኢየሱስ ፍጡር ነው ተብሎ የቀረበው መለኮታዊ ባሕርዩን ገላጭ እና ይልቅም አምላክነቱን የሚያሳይ ሆኖ እናገኘዋለን። ማጣቀሻ [1] Vines Complete Expository Dictionary of Old and New Testament Words, Thomas Nelson Publishers, Nashville Camden New York, 1984, P. 319.

የባሕርዩ ምሳሌ? Read More »

“አንድ ታሪክ ላውጋችሁ”

ከአዲስ አበባ ወጣ ብላ በምትገኝ በአንዲት ገጠራማ አካባቢ የሚኖሩ አነስተኛ ማህበረሰብ ነበሩ። አብዛኛዎቹ የአውራጃው ነዋሪዎች ጣዖት አምላኪያን የነበሩና ስለ እግዚአብሔር መኖር የማያቁ የሆኑ እንደዋዛ የሚታለፉም አይደሉም። በዛ መካከል እውነትን የሚያቁ ጥቂት ክርስቲያኖች ግን አልጠፉም ነበር፡፡ ያው ጭስ ባለበት ጥቂትም ቢሆን እሳት አይጠፋም እንደሚባለው ተረቱ አንዳንድ ቦታዎች ላይ ሰፍረው ነበር።(ከዛ በፊት ሚሶናውያን በስፍራው ተልከው ወንጌልን ያደረሱ የነበሩ ይመስላል።) በጥልቀት በማህበረሰቡ ጫና ምክንያት ግን ወንጌልን ባለማድረሳቸው ብርቱ ክርስቲያን እንቁጠር ብንል እንደ ቦዘና ሽሮ ጥቂት ሥጋ ጣል ጣል ይመስል በትግል ነው የምናገኘው፡፡ (ያው ቦዘና ስለምወድ ምሳሌ ተጠቀምኳት፤ የምትወዱ ሰዎች ካላችሁ ከአፍቃሬ ነኝ ለማለት ነው)። በአንድ ወቅት እኒያ ወንጌልን የሰሙት ሰዎች ላልሰሙ ሰዎች ለማድረስ ለሁለት ተከፍለው ለጣዖት አምላኪውና አንዱ ወገን ደሞ አምላክ የለም(እግዚአብሔርን ለማያቀው) ተበታትነው በአንድነት ማሰራጨት ጀመሩ። በማህበረሰቡ መካከል በብዙ ታወቁ፣ ክርስትና ከዛች መንደር አልፎ ቀያቸውን ሙሉ አጥለቀለቀው፡፡ የዚህ ሁሉ ብርታትና የአንድነታቸው ምክንያት ለቤተክርስቲያን ቀናኢ ሀሳብ አለን ማለታቸውና አንዱ በአንዱ ስራ ጣልቃ ሳይገባ፣ ሳይንቅ፣ የሚሰራውን አገልግሎት ሳያሰናክልና ክፉ ሳያስብ አንድነትን ስለመረጠ ነበር። የሆነው ሁሉ ግን በአንዲት ክፉ ቀን ይሄ አንድነት ብዙ ርቀው እንዳይሄዱና ተሰናክለው እንዲወድቁ አደረጋቸው፡፡ የሰላሟ መንደርም ሁከት ተጀመረ። ለዚህ ሁሉ ጉስቁልና መንስኤ ክፋት ማሰባቸው ነበር። በተጨማሪም ሐዋርያው ጴጥሮስ በክታቡ እንዲህ ያለውን መዘንጋታቸው ነበር፦ “እግዚአብሔርንም በመምሰል የወንድማማችን መዋደድ፥ በወንድማማችም መዋደድ ፍቅርን ጨምሩ።” 2ኛ ጴጥሮስ 1፥7 እግዚአብሔርን ምሰሉ በተባሉበት ቦታ ይልቅ የራስን ፍላጎትን በሰዉ ዘንድ መሳላቸው፣ ከአሻጥር ይልቅ መዋደድን ሳሉ በተባሉበት ቦታ ላይ የእኔ ወንጌል በላጭ የእግዚአብሔሩ ሀሳብም በእኔ ተገልጧልና ፍቅር እኔ ጋር ነው፤ የእርሱ ወንጌል እንዲህ…በማለት ለማህበረሰቡ አልባሌ ስብከት ማሰማት ጀመሩ። ይሄ ነበር የውድቀታቸው ምክንያቱ፡፡ ታሪኩ በዚህ አላበቃም ቢያበቃማ ጥሩ ነበር፤ እነዚያ ወንጌል የሰሙ ያመልኩበትም የነበረችው ቤት በዚህ ሽኩቻ ወደቀች፣ የመንደሪቷ ቤተክርስቲያን ፖለቲካ ስለያዛት ተናደች፣ የአንዱን ግለሰብ ትችት ለገሃዱ ዓለም መናገር የሚያመጣውን ጦስ ስላልተገነዘቡ ጣዖት አምላኪያኑ ወደ እጣናቸውና ደም ማፍሰስ፤ አምላክ የለሾቹ ወደ ቁዘማቸው ገቡ፡፡ ይሄን ሁሉ ታሪክ ያነበብክ አንባቢዬ የነገሩ መጎሳቆል ለምን የሆነ ይመስልሃል? እንዲያ እንዲህ ብለህ ልታብራራ ከቻልክ ጥያቄው ላንተ በዝርዝር ከታች ላስቀምጥልህ፦  ➞ የክርስቲያኖቹ እንዲያ መሆን መንስኤው ምንስ ይሆን? ➞ በዚህስ ዘመን ምን እየሰማህ ይሆን? ➞ በዚህ ታሪክ ላይ ቀይራለሁ ብለህ ምታስበው ነገር ይኖር ይሆን? ኦኦኦ….ጥያቄማ አላብዛ ይቅር፤ ይሄ አጭር ማስታወሻዬ ጽሑፍ ለካ ብዙ ጥያቄ ያግዳል..! ጽሑፏም ጣፍጣ ለአንባቢያን በአጭሩ አትቀርብ ይሆን በሚል አሳጥሬዋለሁ፡፡ አድማጬና አንባቢዬ ሆይ..! ስትመልሳቸው ሐዋሪያው ጨምሩ ማለት ምን ማለት ይሆን? የምትለዋን ነገር ባትረሳት ጥሩ ነው፡፡ ጨረስኩ እያልኩ ቀጠልኩ አይደል ጨርሻለሁ።[2] 1] ሰሞናዊውን የክርስቲያን ማህበረሰብ ሁኔታ ስንመለከት ይሄ ታሪክ ለመጻፍ ተነሳሁ። ከእግዚአብሔር አገልጋይ ሆነው ግን በእግዚአብሔር ዓለም ውስጥ የሌለን ማንነት ለማሳየት፣ ለማጉላት መሞከራቸውን ሳይ እግዜሩ ይፋረድ አልኩና ይሄን አጭር ታሪክ በአጭር ማስታወሻዬ አካተትኩላችሁ። 2] በመጨረሻም ይሄን የጽሑፍ ልጥፍ ለማለት የፈለገውና የተነገረው ሳይገባህ ቅርጫፉን ይዘህ በደፈናው የምትቆጣ፣ ምዕመኑን ጨፍላቂና እብሪተኛ መጋቢ ሆይ….! ቤተክርስቲያን ላይ መንግስት ለመሆን የምታስቡም ጭምር ካላችሁ…! ይቺ አጭር ፖስት ለእናተ ትቀርብልኝ ዘንድ አሳሰብኩ። እግዚአብሔር በዚህ ዘመን ከምንሰማው ነገር ሁሉ ይጠብቀን። አሜን።

“አንድ ታሪክ ላውጋችሁ” Read More »

ይገርማል…ይደንቃል….!

ድንቅ ነው!! አምላክ ሥጋን ለብሶ ወደ ምድር መጣ የሃጥያት መከራችንንና የዲያቢሎስ የሹፈት ነጋሪት ዝም ለማስባልም ተገለጠ። ነገር ግን የእኛን መከታን ነፃ አውጪያችንን፦ በአክሊል ፋንታ የእሾህ ጉንጉን፣ በፍቅር ከማቀፍ ፋንታ ሰጠነው ጅራፍ፣ በእጆቻችን። እሱም አልበቃ ብሎ አዳኙን ራሱን ራስህን አድን አልነው፤ ሙሾ በሚመስል ቅላጼ እያላገድን አሾፍንበት፤ ከዛም ብሶ ሰቀልነውም በእንጨት በችንካር አድርገን። ይሄ ሁሉ ሆነና ጀንበርም ሳትጠልቅ፣ ፀሐይም ሳትገባ ሥራው ድንቅ ነው የሚል ድምጽ ሰማይ ምድር ሁሉ መወደስ ጀመረ። የጩኸቱ ድምድምታ ምን ይሆን? ብለን ተነሳን፤ እኛም ያኔ ጎኑን የተወጋው፣ እጆቹም ተቸነከሩ፣ ሄዷልና ሞቷል የተባለው አዳኙ ራሱ ያው መሢህ መሆኑን አወቅን። በፍርሃትም ያየነውን በመገረም ድንቅ ነው አልን። ከእላፋት ጋር አእላፋት ሆነን፥ ባሾፍንበት ከንፍራችን ከሙታን በኩር፣ የነገስታት ንጉስ፣ የጌቶች ጌታ፣ የምድር ሁሉ ባለቤት እርሱን አመሠገንን። ጨመር አድርገንም ተነስቷል በዚህ የለም መቃብሩ ባዶ ነው ተመልከቱ በዚህ የለም፤ በሚል ክብሩ ሁሉ በአርያም በምድር ይሁን ስንል ጣፋጭ መዓዛ ያለውን ዝማሬ ለታረደው በግ አቀረብን። ለአንባቢው መልዕክቴ በዚህ ወቅት ላይ የጥሞና ጊዜ ያጣህ እና ረፍት የሌለህ ሆይ “እርሱ ሰላም የሚሰጥ እረፍት ነውና በልብህ ታስገባው ዘንድ አሳሰብኩህ”። አሜን።[፩][፪][፫] መልካም የጥሞና ጊዜ ይሁንላችሁ…..! [፩] ከሚባለው በላይ ከደረሰበት መከራ አንጻር ይገርማል ጥቂት ሆና ትታየን ዘንድ አንባቢው ያስተውል። [፪] ይደንቃል ስንል ከእውነት የሆነ መደነቅ እንዲሆን ሰሚው ከንግግል ባለፈ ከልብ በኾነ ፍቅር ትል እንደሆን አሳሰብኩህ። [፫] ምንጭ፦ አጭር ማስታወሻ በወንድም David Yeshua, ያልታተመ በጽሑፍ ላይ ካለ መጣጥፍ የተወሰደ።

ይገርማል…ይደንቃል….! Read More »

Scroll to Top