ለሙስሊም ሰባክያን ሙግት ምላሽ ሰሞኑን በሙስሊሞች ዘንድ በማህበራዊ ሚዲያ ሲሰራጩ ከነበሩ ሙግቶች መካከል አንዱ ተከታዩ አንድ ሙስሊም የጻፈው ጽሑፍ ነው። የዚህ ጽሑፍ አዘጋጅ የዕውቀቱ ልክ በጽሑፎቹ ውስጥ የሚታየው ከሆነ ራሱን የማስተማር ብቃት እንዳለው ሰው በመቁጠር ለመጻፍ መድፈሩ፤ አንባቢያኑም ደግሞ ይህንን ሙግት ከቁም ነገር ቆጥረው መቀበላቸው የሚያሳዝን ነው። ሙግቱም እንዲህ ሲል ይጀምራል፦ አብዱል በአሏህ ስም እጅግ በጣም ሩኅሩህ እጅግ በጣም አዛኝ በሆነው፡፡ 112፥3 «አልወለደም አልተወለደምም»፡፡ ጥንት ላይ የነበሩ ነቢያት እንዲሁ ኢየሱስ እና ሐዋርያት አሓዳዊያን”Unitarian” የነበሩ ሲሆን ከሐዋርያት ኅልፈት በኃላ የተነሱ የቤተክርስቲያን አበው ደግሞ በሂደት “ክልዔታውያን”Binitarian” ነበሩ። ከክልዔታውያን አበው መካከል ጠርጡሊያኖስ”Tertullian” ስለ ወልድ ሲናገር እንዲህ ይለናል፦ “አብ አጠቃላይ ባሕርይ ነው፥ ነገር ግን ወልድ የአጠቃላዩ መገኘት እና ክፍል ነው” (Against Praxeas (Tertullian), Chapter 9) መልስ የብሉይ ኪዳንን ቅዱሳት መጽሐፍት ስንመለከት እግዚአብሔር አምላክ ነጠላ አንድ ነበረ ማለት አንችልም። ለዚህም ማሳያ መጽሐፍ ቅዱስ በዘፍጥረት 1፥26 እንዲህ ይላልና፦ “እግዚአብሔርም አለ፦ ሰውን በመልካችን እንደ ምሳሌአችን እንፍጠር፤ የባሕር ዓሦችንና የሰማይ ወፎችን፥ እንስሳትንና ምድርን ሁሉ፥ በምድር ላይ የሚንቀሳቀሱትንም ሁሉ ይግዙ።” የእግዚአብሔርን ሥሉስ አሓዳዊነት ከሚያመለክቱ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች መካከል አንዱ ከላይ ያነበብነው ጥቅስ ነው። እግዚአብሔር አብ ዓለማትን በልጁ መፍጠሩን (ዕብ1፥2፤ ዮሐ1፥3፤ ቆላ1፥16-17) እንዲሁም ደግሞ ፍጥረትን በማስገኘት ሒደት ውስጥ መንፈስ ቅዱስ ጉልሕ አስተዋጽኦ እንደነበረው ቅዱሳት መጻሕፍት አበክረው ይነግሩናል (ዘፍ 1፥3 ፤ ኢዮ33፥4)። በዘፍጥረት 1፥26 ላይም በብዙ ቁጥር ግስ “እንፍጠር” (נַעֲשֶׂה “ናዓሴህ”)፣ በብዙ ቁጥር ስሞች “በመልካችን” (בְּצַלְמֵ֖נוּ “ቤጻልሜኑ”) እንዲሁም “ምሳሌአችን” ( כִּדְמוּתֵנוּ ”ኪድሙቴኑ”) ማለቱ አሐዱ ሥሉስን እንደሚያመለክት በርካታ የመጽሐፍ ቅዱስ ምሑራን የሚስማሙበት እውነታ ነው፡፡ በዚህ ርዕሰ ጉዳይ ላይ በገጻችን የጻፍነው ጽሑፍ መመልከት ይቻላል።[1] ይህ ሙስሊም ጸሐፊ ቀጠል አድርጎ የቤተክርስቲያን አበው ሥላሴያውን አልነበሩም ብሎ በድፍረት ይናገራል። ነገር ግን ይህ ፍጹም ሐሰት እና ቅጥፈት ነው። ይባስ ብሎ ጠርጡሊያኖስንም ጨምሮ የጥንት ቤተክርስቲያን አባቶች “Binitarian” ናቸው ይለናል። በዚህ ንግግሩ ጸሐፊው የቤተክርስቲያን ታሪክ እውቀት የለውም ወይም ደግሞ ሆነ ብሎ አንባቢያኑን እየዋሸ ነው ማለት ነው። ሙስሊሙ ወገናችን ላነሳው ሀሳብ ምላሽ ከመስጠታችን በፊት በትምህርተ ሥላሴ ላይ የቤተ-ክርስቲያን አበው የነበራቸው አቋም ጥርት ያለ እንደነበር እስኪ በጥቂቱ እንመልከት፦ 1) ፖሊካርፕ (Polycarp):- በ70ዓ.ም ተወልዶ በ155 ዓ.ም ወይም በ160 ዓ.ም የሞተ፣ የሐዋሪያው ዮሐንስ ደቀ መዝሙር የነበረ ሲሆን የሰምርኔስ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ የነበረ ሰው ነው። ትምህርተ ሥላሴን በተመለከተ እንዲህ ይላል፦ ሁሉን ቻይ እግዚአብሔር ሆይ…ዘላለማዊና ሰማያዊ በሆነ ሊቀ ካህናት፣ በምትወደውና ባከበርኸው ልጅህ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ለአንተና ለእርሱም እንዲሁም ለመንፈስ ቅዱስ አሁንም ሆነ ለዘላለም ክብር ይሁን[2] 2) ዮስጢኖስ ሰማዕት(Justin Martyr) ፦ በቤተክርስቲያን የእምነት ተሟጋችና አቃቤ እምነት የነበረው ይህ አባት በ100 ዓ.ም ተወልዶ በ165 ዓ.ም እንደሞተ ይገመታል። ይህ አባት በአቅብተ እምነት ጽሑፉ ላይ ትምህርተ ሥላሴን በተመለከተ እንዲህ በማለት ጽፏል፦ የዓለማት ጌታ በሆነው በእግዚአብሔር አብ፣ በመድሐኒታችንም ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲሁም በመንፈስ ቅዱስ ስም በውሃ መታጠብን ያገኛሉ።[3] 3) አግናጢዮስ ዘአንጾኪያ(Ignatius of Antioch) ፦ የአንጾኪያ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ የነበረና ከ98 ዓ.ም እስከ 117 ዓ.ም መካከል ሰማዕት እንደሆነ የሚነገርለት አባት ክርስትናን ከመናፍቃን በመከላከሉ ዙሪያ ብዙ የጻፈ ዐቃቤ ክርስትና ነው። ትምህርተ ሥላሴን በተመለከተ እንዲህ በማለት ጽፏል፦ በጌታችንና በሐዋርያት ትምህርት እድትጸኑ፣ የምታደርጉት ነገር ሁሉ በስጋና በመንፈስ እንዲከናወንላችሁ፣ በእምነትና በፍቅር፤ በወልድ፣ በአብና በመንፈስ ቅዱስ፣ በመጀመሪያው እና በመጨረሻው፤ ከተወደደው ጳጳሳችሁ፣ በጎ ከሆነው የሽማግሌአችሁ መንፈሳዊ አክሊል፣ እናም እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ካሉ ዲያቆናት ጋር አጥኑ። በስጋችሁም በመንፈሳችሁም አንድነት እንዲኖራችሁ ክርስቶስ ኢየሱስ ለአብ በስጋው እንደተገዛለት፣ ሐዋርያት ለክርስቶስ ለአብ እና ለመንፈስ ቅዱስ እንደተገዙ፣ እናንተም ለጳጳሳችሁ እና እርስ በእርሳችሁ ተገዙ(ታዘዙ)። [4] 4) ጠርጡሊያኖስ ወይም ተርቱሊያን (Tertullian 160-215) አፍሪካዊ ዕቃቤ ክርስትና እንዲሁም የነገረ መለኮት ሊቅ ነው። የጥንቷ ቤተ ክርስቲያን አባት የሆነው ጠርጡሊያኖስ በሥላሴያዊ አስተምህሮ ላይ ለሚነሱ ኑፋቄዎች መልስ በመስጠትና በክርስቲያናዊ ሥነ-መለኮት ከሚሰሩ አቃብያነ አባቶች መካከል አንዱ ነው። ለምሳሌ በመናፍቃን ሙግት ላይ ባነሳው በፕራክሲየስ (against praxeas) የሞዳሊዝም አራማጅ የሆነው የፓትሪፓሺያን(Patripassian) ሐሳብ አንስቶ እንዲህ ሲል በሙግቱ ላይ ጽፏል፡- ሶስቱ አብ፣ ወልድና መንፈሱ ናቸው። ሶስት ናቸው። ነገር ግን በሁናቴ አይደለም በግብር እንጂ፤ በኑባሬም አይደለም በአካል እንጂ፤ በስልጣን ወይም በሐይል አይደለም በገጽታ እንጂ ሆኖም ግን እግዚአብሔር አምላክ አንድ ኑባሬ፣ ስልጣን፣ ሐይል አለው ምክንያቱም በአካል፣ በግብርና በአይነት በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ የተገለጠ አንድ አምላክ ነውና..[5] እንግዲህ ጠርጡሊያኖስ እና ሌሎች በርካታ አበው አብ፣ ወልድና መንፈስ ቅዱስ ከዘላለም ያለመሽቀዳደም እንዲሁም ያለመነጣጠል አሐዱ ሥሉስ እንደነበሩ ይነግሩናል። እንደ ሮሙ ቀለሜንጦስ(30-95)፣ ሔሬኒየስ (115-190) እና ቀጰዶቃውያን አበው (Cappadocian Fathers) ያሉ የቂሳርያው ትልቁ አባት ባስልዮስ፣ ጎርጎርዮስ ዘንዚናዙ፣ ጎርጎሪዮስ ዘኑሲስ እንዲሁም ሌሎች የቤተክርስቲያን አባቶች እንዘርዝር ብንል ትምህርተ ሥላሴን በተመለከተ በድርሳናቸው የጻፉትን እልፍ መረጃ እናገኛለን። ስለዚህ ሙስሊሙ ጸሐፊ “የቤተክርስቲያን አባቶች ስለ ሥላሴ ግንዛቤ የላቸውም ይልቅ አብና ወልድን ብቻ ጠቅሰው መንፈስ ቅዱስ ህልውና የለውም ብለዋል” በማለት “ክልዔታውያን “Binitarian” ነበሩ” በማለት በጽሑፉ ያሰፈረው ፈጽሞ ከእውነት የራቀ ነው። ይህን መሠል ሙግት ደሞ ከላይ ባስቀመጥናቸው የአባቶች ትምህርት ውድቅ ይሆናል። በመቀጠል ይህ ሙስሊም ጸሐፊ ሙግቴን ይደግፋል በማለት የአርዮሳውያንን ሙግት በመውሰድ ለመሞገት ሲጣደፍ ይስተዋላል። ሙስሊሙ ጸሐፊ ይህንን ሀሳቡን ለመደገፍ የጠቀሰው የጠርጡሊያኖስ ሥራ ከሆነው “Against Praxeas” ከተሰኘው ጽሁፍ ነው። ይህ አባት በጽሑፉም ሆነ በቃል የሥላሴን ትምህርት እውነተኝነት እየተሟገተ እና የሞዳሊዝምን (አብ፣ ወልድ እና መንፈስ አንድ ነጠላ አካል ነው ለሚሉ) ትምህርት አቀንቃኝ መናፍቃን እየሞገተ የጻፈው ጽሁፍ ነው። በዚህ ዐውደ-ጽሑፍ ጠርጡሊያኖስ የሚከራከረው በሦስት አካል ስለተገለጠው አንዱ መለኮት ነው። በምዕራፍ 9 ሙሉ አውዱ እንዲህ ሲል ይጽፋል፦ “Bear always in mind that this is the rule of faith which I profess; by it, I testify that the Father, and the Son, and the Spirit are inseparable from each other, and so will you know in what sense this is said. Now, observe, my assertion is that the Father is one, and the Son one, and the Spirit one, and that They are distinct from Each Other. This statement is taken in a wrong sense by every uneducated as well as every perversely disposed person, as if it predicated a diversity, in such a sense as to imply a separation among the Father, and the Son, and the Spirit.” “እኔ የምመሰክረው የእምነት መርህ ይህ መሆኑን ልብ በሉ። በዚህም አብ፣ ወልድና መንፈስም የማይነጣጠሉ እንደ ሆኑ እመሰክራለሁ። ነገር ግን በምን መንገድ ይህ እንደሚባል አስተውሉ። እንግዲህ የኔ ሙግት “አብ አንድ እንደ ሆነ፣ ወልድም አንድ እንደሆነ፣ መንፈስም አንድ እንደ ሆነ፤ ነገር ግን እርስ በርሳቸውም ልዩ (distinct) እንደ ሆኑ ነው። ይሄም አገላለጽ ባልተማረ ሁሉ እንዲሁም ጠማማ አስተሳሰብ ባላቸው ሰዎች ሁሉ በተሳሳተ መንገድ ይወሰዳል። በአካላቱ[በአብ፣ በወልድ እና በመንፈስ] መካከል መለያየትን እንዳለብ በሚያመለክት መልኩ ብሎም በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ መካከል መነጣጠል እንዳለ በማሳየት አጣምመው ይተረጉማሉ።[6] ሙስሊሙ ጸሐፊም ከላይ ጠቅሶ የጻፈው በዚህ ምዕራፍ ውስጥ የተጠቀሰ ሲሆን። ከአውዱ ውጭ ገንጥሎ በማውጣት ለአንባቢያኑ ጽፎላቸዋል። የጠርጡሊያኖስ ጽሁፍ እንዲህ ይነበባል፦ “Thus the Father is distinct from the Son, being greater than the Son, in as much as He who begets is one, and He who is begotten is another; He, too, who sends is one, and He who is sent is another; and He, again, who makes is one, and He through whom the thing is made is another……..Lord