Trinity

የሥላሴ ሥነ አመክንዮአዊ ችግር(LPT)

የሥላሴ አስተምህሮ በተለያዩ ሰዎች በተለያዩ ዘመናትም ትችት ሲደርስበት መስማት የተለመደ ነው። ይህንንም ትምህርት በሰዎች አእምሮ ዘንድ ፈጽሞ መረዳት የማይቻልና በተለይም “አምላክ/God/” የሚለውን ቃል በተለያዩ አይነት በመጠቀም በሥነ አመክንዮ ዘንድ መሠረታዊ ችግር እንዳለበት ለማሳየት ይሞክራሉ። ሙግቱ እንዲህ ይቀርባል፦ 1) ክርስቲያኖች አብ አምላክ ነው፣ ወልድ አምላክ ነው፣ መንፈስ ቅዱስ አምላክ ነው ይላሉ። 2) ነገር ግን “አምላክ” የሚለው ቃል በአንድ ጊዜ አብን፣ ወልድን እንዲሁም መንፈስን የሚያመለክት ከሆነ አንድን ምንነት ያለውን አምላክ በቋሚነት ሊያመለክት አይችልም። 3) ስለዚህ ይህ አስተምህሮው ከአመክንዮአዊ ወጥነት ይልቅ አሻሚ የሆነ ግራ አጋቢ ትርጉም ላይ እንዲሆን ያደርገዋል። መልስ ይህ ሙግት መሠረት ያደረገው እኛን(ክርስቲያኖችን) “አምላክ” የሚለውን ቃል የተለያዩ አካላትን በተለያየ መንገድ መገለጫ እንደሆነ በማመልከት እንደምንል አድርጎ ሙጉቱን በሥሑት ነጥቦች ላይ ገንብቶ የጀመረ ነው። ማለትም “አምላክ” አብን በአንድ መንገድ፣ ወልድን በሌላ ፣ እንዲሁም መንፈስ ቅዱስን በሌላ እንደማለት ነው። ነገር ግን ይህ አይነቱ መረዳት በሥላሴ የአምላክነት ባሕርይ ወይም “ግጻዌ መለኮት” መረዳት ውስጥ የማያታወቅ ነው። ታዲያ አምላክ ማለት ግን በኑባሬው ያለማቋረጥ አንድ፣ የማይከፋፈል መለኮታዊ ማንነትን የሚያመለክት መለኮታዊ ባህርይ የሚል ቃል ነው። ስለዚህ ክርስቲያኖች “አብ አምላክ ነው”፣ “ወልድ አምላክ ነው” እንዲሁም “መንፈስ አምላክ ነው” ሲሉ የአምላክነት ባህርይን ያለውን አካላቶቹ አሏቸው በዚህም እያንዳንዱ አካል ያንን የመለኮትነትን ባህርይ ሙሉ በሙሉ ይጋራሉ ማለታቸው ነው። ይህም አንድ አምላክ ብቻ አለ ሲባል፣ አንድ ምንነት እንዳለ እያረጋገጡ ነው። አንዱ አምላክ በሦስት አካል የተገለጠ ነው ሲሉ ደግሞ አንድ አምላክ በአካል ሦስት ነው እያሉ ነው። አብ፣ ወልድ እና መንፈስ አንድ አምላክ ናቸው ሲሉ እያንዳንዱ አካል መለኮታዊ ባህርይ እንዳለው እያስረገጡ ነው። ስለዚህ፣ ከላይ በሥላሴ ላይ በተነሳው የሶስቱ ነጥብ ሙግቶች፣ “አምላክ” የሚለውን ቃል ውይይት ከመገባቱ በፊት ከተብራራ፣ የሚመጣውን የትኛውንም ጥያቄ ይመልሳል ማለት ነው።

የሥላሴ ሥነ አመክንዮአዊ ችግር(LPT) Read More »

የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነት

ክፍል 1 “እርሱ በባሕርዩ አምላክ ሆኖ ሳለ፣ ከእግዚአብሔር ጋር መተካከልን ሊለቀው እንደማይገባ አድርጎ አልቈጠረውም፤”  — ፊልጵስዩስ 2፥6 (አዲሱ መ.ት) አንድ አካል አምላክ ነው የሚባለው ወይም እንደ አምላክ ሊመለክ የሚገባው አምላክ ነኝ ብሎ ስለተናገረ ብቻ ወይም ብዙዎች አምላክነቱን ስላወጁለት አይደለም። በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ አምላክ ነኝ ብለው የተነሱ ነገሥታትን እንመለከታለን። ለምሳሌ፦ የጢሮስ ንጉስ እኔ አምላክ ነኝ ማለቱን(ሕዝቅኤል 28፥2-9) ስንመለከት ይህ ንጉሥ እኔ አምላክ ነኝ ስላወጀ ብቻ አምላክ ነው ብሎ መፈረጅ ፈጽሞ አይቻልም። በሰውም አጀብ አንድ አካል አምላክ ስለተባለም አምላክ ሊሆን አይችልም። ምክንያቱም የግሪክ ጣዖታት እንዲሁ ተብለው ምንነታዊ ለውጥ ስላላሳዩን። ክርስቶስ ኢየሱስ አምላክ ለመሆኑ የአምላክነት ግብሩን፤ ባህሪዎቱንና ሐልዎቱን በተለያየ መንገድ መጽሐፍ ቅዱስ ሲናገር፤ ኑባሬውን ሲተርክና ሲገልጽልን እንመለከተዋለን። ከእነዚህም የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ውስጥ አንደኛው የፊልጵስዩስ መልእክት ም2 ቁ6-7 ነው፦ ⁶ እርሱ በባሕርዩ አምላክ ሆኖ ሳለ፣ ከእግዚአብሔር ጋር መተካከልን ሊለቀው እንደማይገባ አድርጎ አልቈጠረውም፤ ⁷ ነገር ግን የባሪያን መልክ ይዞ፣ በሰውም አምሳል ተገኝቶ፣ ራሱን ባዶ አደረገ” ፊልጵስዩስ 2 (አዲሱ መ.ት) ὃς ἐν μορφῇ θεοῦ ὑπάρχων οὐχ ἁρπαγμὸν ἡγήσατο τὸ εἶναι ἴσα θεῷ, Προς Φιλιππησιους 2:6 በጽርዑ ሞርፌ/μορφῇ የሚለው ቃል ኑባሬያዊ መገኘትን፣ ሁናቴን ወይም ባህሪዎተ መልክን የሚገልጽ ቃል ሲሆን ክርስቶስ ኢየሱስ (ወልድ) እም ቅድመ አለም በኑባሬው በባህሪዎተ መልኩ ራሱ አምላክ ሆኖ የሚኖር አካል እንደሆነ ይገልጻል። በተጨማሪም በባለቤትነት ሙያ (Nominative case) የመጣው ሁፓርኾን/ὑπάρχων የሚለው ቃል በአሁን ጊዜ አመልካች ግስ(Present participle tense) መምጣቱ ወልድ ከዘላለም ጀምሮ ከአብ ጋር አብሮ ህያው አብሮ እኩል አብሮ ዘላለማዊ እንደሆነ በሚገልጽ መልኩ እንደመጣ የክፍሉን ሰዋሰው ይነግረናል። ይህም ደግሞ ለወልድ ኑባሬ ጅማሮ አለው ፍጡር እንጂ ፈጣሪ አይደለም ለሚሉት አርዮሳውያን እና ኢብዮናውያን (Ebionite/Ἐβιωναῖοι) በተለምዶው አዶፕሽኒስቶች የሚባሉት የምን*ፍቅና የአስተምህሮቶችን መሰረታቸውን የሚንድ ክፍል ነው። ሙግታችንን ጠበቅ ለማድረግ ያክል ከተመለከትን ደግሞ ወልድ አምላካዊ ባህሪ ከጥንተ ዘላለም ጀምሮ በዚሁ መልክ ሲኖር የነበረው አምላክ ወደ ፈጠራት ጠባበ አለም የሰውን ወይም የባሪያን ባህሪ(መልክ) ይዞ መምጣቱ “ከእግዚአብሔር አብ ጋር መተካከልን ሊለቀው እንደማይገባ አድርጎ አልቈጠረውም” በማለት ብርሃነ አለም ቅዱስ ጳውሎስ ፍንትው አድርጎ የወልድን መለኮታዊ ባህሪዎት ከእግዚአብሔር አብ ጋር እኩል እንደሆነ ያሳየናል። ከአምላክ ጋር እኩል መሆን ወይም በጽርዑ ቶ ኢናይ ኢሳ ቴኦ/τὸ εἶναι ἴσα θεῷ የሚለው ሐረግ እግዚአብሔር ወልድ ከእግዚአብሔር አብ ጋር በባህሪው እኩል ወይም አንድ አይነት ሆሙስዮስ/ὁμοούσιος እንደሆነ በግልጽ ሁኔታ ሲነግረን የአርዮሳውያንን መርሆተ ቃል የሆነውን ተመሳሳይ ወይም ተቀራራቢ ባህሪዎት ሆሞዮስዮስ/ὁμοιούσιος የሚለውን ምንፍቅና አፈር ከመሬት የሚደባልቅ ክፍል እንደሆነ እንመለከታለን። በቁጥር ሰባትን አንድ በአንድ ስንመለከተው “የባሪያን መልክ ይዞ” የሚለው ሐረግ በፊት የተገለጠበት ቅድመ ኑባሬያዊ ባህሪዎት እንደነበረው ቁልጭ አድርጎ ያሳየናል፤ እርሱም በቁጥር 6 ላይ እንዳየነው የወልድ አምላካዊ መልክ (ባህሪ) ከጥንተ ዘላለም ጀምሮ ገንዘቡ የሆነ ምንነት ነው። “በሰውም ምሳሌ ሆኖ” የሚለው አገላለጽ ደሞ ወደ ምድር በመጣ ጊዜ ፈጣሪ በፍጡራን ምሳሌ ሆኖ ሰዋዊ ባህሪዎትን እንደተላበሰ ያሳየናል። ቀጥሎም “ራሱን ባዶ አደረገ” የሚለው ደሞ አንድ ነገር ባዶ ሆነ የሚባለው ያ ነገር መጀመሪያውኑ የሆነ ነገር ሲኖረው ነው። ክርስቶስ ኢየሱስ ደግሞ ራሱን ባዶ አደረገ ሲባል አምላካዊ ሙሉነት የነበረው አካል ወደ ፈጠረው፣ ወዳዘጋጀው፣ ሰዋዊ ባህሪዎት ዝቅ ብሎ በመምጣቱ ነው። ስለዚህ ክርስቶስ ኢየሱስ ሰው ሁኖ ከመምጣቱ በፊት በአምላካዊ ሙሉነት የሚኖር አምጻኤ ኩሉ አምላክ እንደሆነ እንመለከታለን። በመጨረሻም የክርስቶስን አምላክነት የማያምኑ እንዲህ ሲሉ፦”…ክርስቶስ ኢየሱስ (ወልድ) በእግዚአብሔር ወይም በአምላክ መልክ መኖሩ አዳም በእግዚአብሔር መአልክና ምሳሌ በተፈጠረበት ሒሳብና ቀመር ነው…” ይሞግታሉ። ነገር ግን የሁለቱን ክፍሎች የጽርዑን የቃላት አገባብ እና አውዳዊ ምልከታ ባደረግን ጊዜ ፈጽመው የየቅል ሐሳብ እንደሆነ እንረዳለን፦ እግዚአብሔርም አለ፦ ሰውን በመልካችን እንደ ምሳሌአችን እንፍጠር/καὶ εἶπεν ὁ θεός Ποιήσωμεν ἄνθρωπον κατ᾽ εἰκόνα ἡμετέραν καὶ καθ᾽ ὁμοίωσιν…>>  — ዘፍጥረት 1፥26 በዘፍጥረት 1፥26 መልክ ብሎ የገባው የግሪኩ ቃል ኤይኮና/εἰκόνα ሲሆን ምሳሌ የሚለው ደሞ ሆሞዮሲን/ὁμοίωσιν በሚለው የቃላት አገባብ እንደተሰደረ እንመለከታለን። ኤይኮና/εἰκόνα የሚለው ቃል ኤይኮን/εἰκών ማለትም ምስለ መልክን መመሳሰል ወይም መቀራረብ(በውጫዊ ማንነት መገለጫ) የሚል ትርጉም አለው። እግዚአብሔር አምላክ ሰውን በእኛ መልክ(ኤይኮና ሄሜቴራን/εἰκόνα ἡμετέραν) እንፍጠር ሲል በጽድቅና ቅድስና(ኤር 4:24)፤ እንዲሁም በመገንዘብ ችሎታንና እውቀትን(ቆላ 3:10) የመሳሰሉትን የምስስሎሽ መገለጫዎች በሚገልጽ አገባብና አግባብ መምጣቱ ቅብል ነው። ነገር ግን የሰው ልጅ በእግዚአብሔር መልክና አምሳል መፈጠሩ በእርግጥ የሚካፈለው ባህሪ እንዳለው ሁሉ የማይካፈለው ባህሪ አለ። በዛው በፊልጵስዩስ መልእክት 1:7 እና 2ኛ ጴጥሮስ 1፥4 ላይ የእግዚአብሔር የባህሪው ተካፋዮች እንደሆንን ይናገራል፦ “ስለ ክፉ ምኞት በዓለም ካለው ጥፋት አምልጣችሁ ከመለኮት ባሕርይ ተካፋዮች(κοινωνοὶ φύσεως) በተስፋ ቃል እንድትሆኑ፥ በእነዚያ ክብርና በጎነት የተከበረና እጅግ ታላቅ የሆነ ተስፋን ሰጠን።”2ኛ ጴጥሮስ 1፥4 ተካፋይ ወይም በግሪኩ ኮይኖኖስ/κοινωνός የሚለው ቃል የሰው ልጅ ከእግዚአብሔር ፈጽሞ የማይካፈለው ወይም የቀረበት ነገር እንዳለ አመላካች ነው። ይህንን ሐሳብ በሌላ ክፍል በስፋት እንመለከተዋለን። ነገር ግን ክርስቶስ ኢየሱስ ከእግዚአብሔር አብ ጋር የማይጋራው ሆነ የማይካፈለው ባህሪ የለም። ከላይ በፊልጵስዩስ መልእክት 2:6 ከአብ ጋር በመለኮተ ባህሪዎት እኩል ወይም አንድ እንደሆነ ተመልክተናል። ስለዚህ አምላክ ክርስቶስ ኢየሱስ በአምሳለ ሰውነት መገለጡ (እንደ ሰው መብላት መጠጣቱ፤ መተኛት መነሳቱ፤ መወለድ ማደጉ ወዘተ) መለኮታዊ ክብር እንደሌለው የሚያሳየን ተግባር አይደለም። እርሱ ወደዚች ወደ ፈጠራት አለምና ሰውነት ከመገለጡ በፊት አምላካዊ ምንነት፤ ክብርና መለኮታዊ ኑባሬ ከጥንተ ዘላለም ጀምሮ ገንዘቡ ያደረገ ኃያል አምላክ ነው።

የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነት Read More »

የኒቂያ ጉባኤ እና ጥንታዊያን አበው

ለሙስሊም ሰባክያን ሙግት ምላሽ ሰሞኑን በሙስሊሞች ዘንድ በማህበራዊ ሚዲያ ሲሰራጩ ከነበሩ ሙግቶች መካከል አንዱ ተከታዩ አንድ ሙስሊም የጻፈው ጽሑፍ ነው። የዚህ ጽሑፍ አዘጋጅ የዕውቀቱ ልክ በጽሑፎቹ ውስጥ የሚታየው ከሆነ ራሱን የማስተማር ብቃት እንዳለው ሰው በመቁጠር ለመጻፍ መድፈሩ፤ አንባቢያኑም ደግሞ ይህንን ሙግት ከቁም ነገር ቆጥረው መቀበላቸው የሚያሳዝን ነው። ሙግቱም እንዲህ ሲል ይጀምራል፦ አብዱል በአሏህ ስም እጅግ በጣም ሩኅሩህ እጅግ በጣም አዛኝ በሆነው፡፡ 112፥3 «አልወለደም አልተወለደምም»፡፡ ጥንት ላይ የነበሩ ነቢያት እንዲሁ ኢየሱስ እና ሐዋርያት አሓዳዊያን”Unitarian” የነበሩ ሲሆን ከሐዋርያት ኅልፈት በኃላ የተነሱ የቤተክርስቲያን አበው ደግሞ በሂደት “ክልዔታውያን”Binitarian” ነበሩ። ከክልዔታውያን አበው መካከል ጠርጡሊያኖስ”Tertullian” ስለ ወልድ ሲናገር እንዲህ ይለናል፦ “አብ አጠቃላይ ባሕርይ ነው፥ ነገር ግን ወልድ የአጠቃላዩ መገኘት እና ክፍል ነው” (Against Praxeas (Tertullian), Chapter 9) መልስ የብሉይ ኪዳንን ቅዱሳት መጽሐፍት ስንመለከት እግዚአብሔር አምላክ ነጠላ አንድ ነበረ ማለት አንችልም። ለዚህም ማሳያ መጽሐፍ ቅዱስ በዘፍጥረት 1፥26 እንዲህ ይላልና፦ “እግዚአብሔርም አለ፦ ሰውን በመልካችን እንደ ምሳሌአችን እንፍጠር፤ የባሕር ዓሦችንና የሰማይ ወፎችን፥ እንስሳትንና ምድርን ሁሉ፥ በምድር ላይ የሚንቀሳቀሱትንም ሁሉ ይግዙ።” የእግዚአብሔርን ሥሉስ አሓዳዊነት ከሚያመለክቱ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች መካከል አንዱ ከላይ ያነበብነው ጥቅስ ነው። እግዚአብሔር አብ ዓለማትን በልጁ መፍጠሩን (ዕብ1፥2፤ ዮሐ1፥3፤ ቆላ1፥16-17) እንዲሁም ደግሞ ፍጥረትን በማስገኘት ሒደት ውስጥ መንፈስ ቅዱስ ጉልሕ አስተዋጽኦ እንደነበረው ቅዱሳት መጻሕፍት አበክረው ይነግሩናል (ዘፍ 1፥3 ፤ ኢዮ33፥4)። በዘፍጥረት 1፥26 ላይም በብዙ ቁጥር ግስ “እንፍጠር” (נַעֲשֶׂה “ናዓሴህ”)፣ በብዙ ቁጥር ስሞች “በመልካችን” (בְּצַלְמֵ֖נוּ “ቤጻልሜኑ”) እንዲሁም “ምሳሌአችን” ( כִּדְמוּתֵנוּ ”ኪድሙቴኑ”) ማለቱ አሐዱ ሥሉስን እንደሚያመለክት በርካታ የመጽሐፍ ቅዱስ ምሑራን የሚስማሙበት እውነታ ነው፡፡ በዚህ ርዕሰ ጉዳይ ላይ በገጻችን የጻፍነው ጽሑፍ መመልከት ይቻላል።[1] ይህ ሙስሊም ጸሐፊ ቀጠል አድርጎ የቤተክርስቲያን አበው ሥላሴያውን አልነበሩም ብሎ በድፍረት ይናገራል። ነገር ግን ይህ ፍጹም ሐሰት እና ቅጥፈት ነው። ይባስ ብሎ ጠርጡሊያኖስንም ጨምሮ የጥንት ቤተክርስቲያን አባቶች “Binitarian” ናቸው ይለናል። በዚህ ንግግሩ ጸሐፊው የቤተክርስቲያን ታሪክ እውቀት የለውም ወይም ደግሞ ሆነ ብሎ አንባቢያኑን እየዋሸ ነው ማለት ነው። ሙስሊሙ ወገናችን ላነሳው ሀሳብ ምላሽ ከመስጠታችን በፊት በትምህርተ ሥላሴ ላይ የቤተ-ክርስቲያን አበው የነበራቸው አቋም ጥርት ያለ እንደነበር እስኪ በጥቂቱ እንመልከት፦ 1) ፖሊካርፕ (Polycarp):- በ70ዓ.ም ተወልዶ በ155 ዓ.ም ወይም በ160 ዓ.ም የሞተ፣ የሐዋሪያው ዮሐንስ ደቀ መዝሙር የነበረ ሲሆን የሰምርኔስ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ የነበረ ሰው ነው። ትምህርተ ሥላሴን በተመለከተ እንዲህ ይላል፦ ሁሉን ቻይ እግዚአብሔር ሆይ…ዘላለማዊና ሰማያዊ በሆነ ሊቀ ካህናት፣ በምትወደውና ባከበርኸው ልጅህ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ለአንተና ለእርሱም እንዲሁም ለመንፈስ ቅዱስ አሁንም ሆነ ለዘላለም ክብር ይሁን[2] 2) ዮስጢኖስ ሰማዕት(Justin Martyr) ፦ በቤተክርስቲያን የእምነት ተሟጋችና አቃቤ እምነት የነበረው ይህ አባት በ100 ዓ.ም ተወልዶ በ165 ዓ.ም እንደሞተ ይገመታል። ይህ አባት በአቅብተ እምነት ጽሑፉ ላይ ትምህርተ ሥላሴን በተመለከተ እንዲህ በማለት ጽፏል፦ የዓለማት ጌታ በሆነው በእግዚአብሔር አብ፣ በመድሐኒታችንም ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲሁም በመንፈስ ቅዱስ ስም በውሃ መታጠብን ያገኛሉ።[3] 3) አግናጢዮስ ዘአንጾኪያ(Ignatius of Antioch) ፦ የአንጾኪያ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ የነበረና ከ98 ዓ.ም እስከ 117 ዓ.ም መካከል ሰማዕት እንደሆነ የሚነገርለት አባት ክርስትናን ከመናፍቃን በመከላከሉ ዙሪያ ብዙ የጻፈ ዐቃቤ ክርስትና ነው። ትምህርተ ሥላሴን በተመለከተ እንዲህ በማለት ጽፏል፦ በጌታችንና በሐዋርያት ትምህርት እድትጸኑ፣ የምታደርጉት ነገር ሁሉ በስጋና በመንፈስ እንዲከናወንላችሁ፣ በእምነትና በፍቅር፤ በወልድ፣ በአብና በመንፈስ ቅዱስ፣ በመጀመሪያው እና በመጨረሻው፤ ከተወደደው ጳጳሳችሁ፣ በጎ ከሆነው የሽማግሌአችሁ መንፈሳዊ አክሊል፣  እናም እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ካሉ ዲያቆናት ጋር አጥኑ። በስጋችሁም በመንፈሳችሁም አንድነት እንዲኖራችሁ ክርስቶስ ኢየሱስ ለአብ በስጋው እንደተገዛለት፣ ሐዋርያት ለክርስቶስ ለአብ እና ለመንፈስ ቅዱስ እንደተገዙ፣ እናንተም ለጳጳሳችሁ እና እርስ በእርሳችሁ ተገዙ(ታዘዙ)። [4] 4) ጠርጡሊያኖስ ወይም ተርቱሊያን (Tertullian 160-215) አፍሪካዊ ዕቃቤ ክርስትና እንዲሁም የነገረ መለኮት ሊቅ ነው። የጥንቷ ቤተ ክርስቲያን አባት የሆነው ጠርጡሊያኖስ በሥላሴያዊ አስተምህሮ ላይ ለሚነሱ ኑፋቄዎች መልስ በመስጠትና በክርስቲያናዊ ሥነ-መለኮት ከሚሰሩ አቃብያነ አባቶች መካከል አንዱ ነው። ለምሳሌ በመናፍቃን ሙግት ላይ ባነሳው በፕራክሲየስ (against praxeas) የሞዳሊዝም አራማጅ የሆነው የፓትሪፓሺያን(Patripassian) ሐሳብ አንስቶ እንዲህ ሲል በሙግቱ ላይ ጽፏል፡- ሶስቱ አብ፣ ወልድና መንፈሱ ናቸው። ሶስት ናቸው። ነገር ግን በሁናቴ አይደለም በግብር እንጂ፤ በኑባሬም አይደለም በአካል እንጂ፤ በስልጣን ወይም በሐይል አይደለም በገጽታ እንጂ ሆኖም ግን እግዚአብሔር አምላክ አንድ ኑባሬ፣ ስልጣን፣ ሐይል አለው ምክንያቱም በአካል፣ በግብርና በአይነት በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ የተገለጠ አንድ አምላክ ነውና..[5] እንግዲህ ጠርጡሊያኖስ እና ሌሎች በርካታ አበው አብ፣ ወልድና መንፈስ ቅዱስ ከዘላለም ያለመሽቀዳደም እንዲሁም ያለመነጣጠል አሐዱ ሥሉስ እንደነበሩ ይነግሩናል። እንደ ሮሙ ቀለሜንጦስ(30-95)፣ ሔሬኒየስ (115-190) እና ቀጰዶቃውያን አበው (Cappadocian Fathers) ያሉ የቂሳርያው ትልቁ አባት ባስልዮስ፣ ጎርጎርዮስ ዘንዚናዙ፣ ጎርጎሪዮስ ዘኑሲስ እንዲሁም ሌሎች የቤተክርስቲያን አባቶች እንዘርዝር ብንል ትምህርተ ሥላሴን በተመለከተ በድርሳናቸው የጻፉትን እልፍ መረጃ እናገኛለን። ስለዚህ ሙስሊሙ ጸሐፊ “የቤተክርስቲያን አባቶች ስለ ሥላሴ ግንዛቤ የላቸውም ይልቅ አብና ወልድን ብቻ ጠቅሰው መንፈስ ቅዱስ ህልውና የለውም ብለዋል” በማለት “ክልዔታውያን “Binitarian” ነበሩ” በማለት በጽሑፉ ያሰፈረው ፈጽሞ ከእውነት የራቀ ነው። ይህን መሠል ሙግት ደሞ ከላይ ባስቀመጥናቸው የአባቶች ትምህርት ውድቅ ይሆናል። በመቀጠል ይህ ሙስሊም ጸሐፊ ሙግቴን ይደግፋል በማለት የአርዮሳውያንን ሙግት በመውሰድ ለመሞገት ሲጣደፍ ይስተዋላል። ሙስሊሙ ጸሐፊ ይህንን ሀሳቡን ለመደገፍ የጠቀሰው የጠርጡሊያኖስ ሥራ ከሆነው “Against Praxeas” ከተሰኘው ጽሁፍ ነው። ይህ አባት በጽሑፉም ሆነ በቃል የሥላሴን ትምህርት እውነተኝነት እየተሟገተ እና የሞዳሊዝምን (አብ፣ ወልድ እና መንፈስ አንድ ነጠላ አካል ነው ለሚሉ) ትምህርት አቀንቃኝ መናፍቃን እየሞገተ የጻፈው ጽሁፍ ነው። በዚህ ዐውደ-ጽሑፍ ጠርጡሊያኖስ የሚከራከረው በሦስት አካል ስለተገለጠው አንዱ መለኮት ነው። በምዕራፍ 9 ሙሉ አውዱ እንዲህ ሲል ይጽፋል፦ “Bear always in mind that this is the rule of faith which I profess; by it, I testify that the Father, and the Son, and the Spirit are inseparable from each other, and so will you know in what sense this is said. Now, observe, my assertion is that the Father is one, and the Son one, and the Spirit one, and that They are distinct from Each Other. This statement is taken in a wrong sense by every uneducated as well as every perversely disposed person, as if it predicated a diversity, in such a sense as to imply a separation among the Father, and the Son, and the Spirit.” “እኔ የምመሰክረው የእምነት መርህ ይህ መሆኑን ልብ በሉ። በዚህም አብ፣  ወልድና መንፈስም የማይነጣጠሉ እንደ ሆኑ እመሰክራለሁ። ነገር ግን በምን መንገድ ይህ እንደሚባል አስተውሉ።  እንግዲህ የኔ ሙግት “አብ አንድ እንደ ሆነ፣ ወልድም አንድ እንደሆነ፣ መንፈስም አንድ እንደ ሆነ፤ ነገር ግን እርስ በርሳቸውም ልዩ (distinct) እንደ ሆኑ ነው። ይሄም አገላለጽ ባልተማረ ሁሉ እንዲሁም ጠማማ አስተሳሰብ ባላቸው ሰዎች ሁሉ በተሳሳተ መንገድ ይወሰዳል። በአካላቱ[በአብ፣ በወልድ እና በመንፈስ] መካከል መለያየትን እንዳለብ በሚያመለክት መልኩ ብሎም በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ መካከል  መነጣጠል እንዳለ በማሳየት አጣምመው ይተረጉማሉ።[6] ሙስሊሙ ጸሐፊም ከላይ ጠቅሶ የጻፈው በዚህ ምዕራፍ ውስጥ የተጠቀሰ ሲሆን። ከአውዱ ውጭ ገንጥሎ በማውጣት ለአንባቢያኑ ጽፎላቸዋል። የጠርጡሊያኖስ ጽሁፍ እንዲህ ይነበባል፦ “Thus the Father is distinct from the Son, being greater than the Son, in as much as He who begets is one, and He who is begotten is another; He, too, who sends is one, and He who is sent is another; and He, again, who makes is one, and He through whom the thing is made is another……..Lord

የኒቂያ ጉባኤ እና ጥንታዊያን አበው Read More »

ኃልወተ መንፈስ ቅዱስ

“ብትወዱኝ ትእዛዜን ጠብቁ። እኔም አብን እለምናለሁ ለዘላለምም ከእናንተ ጋር እንዲኖር ሌላ አጽናኝ (ἄλλον παράκλητον) ይሰጣችኋል፤”   ዮሐንስ 14፥15-16 እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ኅልው አምላክ በራሱ የቆመ ማንነት ያለውና ከሥሉሳዊ አካላት መካከል አንዱ አካል ነው። ስለ መንፈስ ቅዱስ አካላዊ ማንነት ከማውራታችን በፊት በተወሰነ መጠን ስለ አካል ምንነት ለመመልከት እንሞክር፦ አካል የምንለው መጠሪያ በጣም ልም ከሆነ ብናኝና በጣም ረቂቅ ከሆነ ትናኝ እጅግ በጣም ረቂቅ ከሆነ አየር ጀምሮ የመጨረሻ ጥጥርነትና ጉልህነት እስካለው ውፍረት ደንዳናነትም ድረስ በዚያ በሚገኝ ዐቅምና ብቃት እንደየ መጠኑ እንደየ መልኩ ተወስኖ እንደሚታወቅ ሁሉ፤ በዓለም ግዘፍ አካል ተብሎ ይሰየማል። በሌላም አገላለጽ በሰማይ ያለው የሚዳሰስና የሚገሰስ የሚቋጠርና በአምስቱ የስሜት ህዋሳት ተደርሶበት የሚጨበት ነገር ሁሉ በዓለመ ግዘፍ አካልነት እንዳለ ያለ መሆኑ ይታወቃልና አካል በሚል ስያሜ መጠራት ገንዘቡ ነው።[1] ነገር ግን አካል የሚለው ስያሜ በአምስቱ ህዋሳት ብቻ ለሚታወቀው ነገር ብቻ ሳይሆን ለማይታይ ለማይዳሰስ፣ ለማይገሰስ፣ ለማይቋጠር ነገር ግን በህያውነት፤ በዓለመ ነፍስ የሚኖር እኔ የሚል ነባቢ ለባዊ አለሁ ባይ ሁሉ አካል አለው ተብሎ ሊጠራ ይችላል።[2] እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ የራሱ የሆነ አካል ያለው አምላክ ነው። መንፈስ ቅዱስ አካል አለው ስንል ከሌላው የስላሴ አካላት ራሱን ችሎ ለራሱ ብቁዕ የሆነ ዕውቀት ቀዋሚነት ያለው አለሁ ባይ ቁመና መሆኑን አመላካች መገለጫ ነው። ከአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ የተለያዩ የምንፍቅና አንጃዎች በመንፈስ ቅዱስ ላይ በተለያየ መንገድ አስተምህሮና ልምምዶች ተነስተው ነበር። በመንፈስ ቅዱስ ላይ ምንፍቅናዊ ዘመቻ የከፈቱትን ቡድኖች ኔውማቶማኪያውያን የሚልን ስያሜን ተሰጥተው ነበር። ኔውማቶማኪ(Pneumatomachi) ወይም በግሪኩ (Πνευματομάχοι) የሚለው ቃል ኔውማ(πνεῦμα) ማለትም መንፈስ እና ማኬ(μάχη) ውጊያ፤ በአንድ አካል ላይ በአሉታዊ ሁኔታ መነሳትን ወይም ጠበኛ መሆንን ሲገልጽ በአጠቃላይ የመንፈስ ቅዱስ ጠበኞች፣ ተቃዋሚዎች አልያም በመንፈስ ቅዱስ ማንነትና ምንነት ላይ በአሉታዊ ጎን የተነሱ ማለት ነው።[3] ለምሳሌ ያክል መቅዶናውያን (የመቅዶኒዮስን አስተምህሮተ ምንፍቅና የሚከተሉ)፣ አርዮሳውያንና ከፊል አርዮሳውያን፣ ሰባልዮሳውያ ወዘተ ተጠቃሽ ናቸው። አንዳንዶቹ የምንፍቅና ቡድኖች የመንፈስ ቅዱስን መለኮትነት ሲክዱ አንዳዶቹ ደግሞ ከነጭራሹን መንፈስ ቅዱስ ህልውና የሌለው ማለትም በራሱ የቆመ ወይም አካል የለውም ብለው ያምናሉ ያስተምራሉ። በዚህ ጽሑፍ መንፈስ ቅዱስን አካላዊ ማንነትን ለሚክዱት ቡድኖች መጽሐፍ ቅዱሳዊ ምላሽን ከሰዋስው እና ከአውዳዊ ዳሰሳ አንጻር አንዳንድ ነጥቦች ለመዳሰስ እንሞክራለን፦ መንፈስ ቅዱስ የራሱ የሆነ ማንነት የለውም “እርሱ የእግዚአብሔር ሐይል ብቻ ነው” ለሚሉ መናፍቃን መጽሐፍ ቅዱሳችን መልስ አለው፦ “ወንጌላችን በኃይልና በመንፈስ ቅዱስ በብዙ መረዳትም እንጂ በቃል ብቻ ወደ እናንተ አልመጣምና፤ በእናንተ ዘንድ ስለ እናንተ እንዴት እንደ ነበርን ታውቃላችሁ።”  — 1ኛ ተሰሎንቄ 1፥5 የተሰሎንቄን መልዕክት ጸሐፊ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ኃይልን(δυνάμει) እና መንፈስ ቅዱስን(πνεύματι ἁγίῳ) በማለያየት “እና(ካይ/καὶ)” በሚለው መስተጻምር ቃላቶቹን ሲሰነጥቃቸው እንመለከታለን። ይህም ማለት መንፈስ ቅዱስ ከኃይል የተለየ ማንነት እንደሆነ ያስረዳል። መንፈስ ቅዱስ በራሱ ኃይል ሳይሆን ኃይልን ባህሪው ያደረገ አምላክ ነው(ሉቃ 4፥14፣ ሐዋ 1፥18፣ ሮሜ 15፥13, 18-19)። በሐዋርያት ስራ ላይ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የመንፈስ ቅዱስን መምጣት ሲናገር መንፈስ ቅዱስን እና ሐይልን ለያይቶ በመናገር እንጂ መንፈስ ቅዱስ ራሱ ሐይል ነው ወይም ሐይል በወረደባችሁ ጊዜ ፈጽሞ አላለም። እንዲያውም መንፈስ ቅዱስ በእነርሱ ላይ በወረደ ጊዜ ሐይልን እንደሚቀበሉ ያስረዳል። ይህም ማለት ሐይል ከመንፈስ ቅዱስ የሚወጣ ባህሪዎት ነው፦ “ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ በእናንተ ላይ በወረደ ጊዜ ኃይልን ትቀበላላችሁ፥ በኢየሩሳሌምም በይሁዳም ሁሉ በሰማርያም እስከ ምድር ዳርም ድረስ ምስክሮቼ ትሆናላችሁ አለ።”  — ሐዋርያት 1፥8 “ብትወዱኝ ትእዛዜን ጠብቁ። እኔም አብን እለምናለሁ ለዘላለምም ከእናንተ ጋር እንዲኖር ሌላ አጽናኝ (ἄλλον παράκλητον) ይሰጣችኋል፤”  — ዮሐንስ 14፥15-16 “ሔቴሮስ/ἕτερος” የሚለው የጽርዕ(ግሪክ) ቃል የተለየ፣ ሌላ ወይም አንድ አይነት ያልሆነ የሚል ትርጉም ሲኖረው አብዛኛውን ጊዜ በአይነትም ሆነ በአካል የተለየን ነገር የሚያመለክት ነው።[4] “አሎስ/ἄλλος” የሚለው የጽርዕ (ግሪክ) ቃል ደግሞ በአይነታቸው ተመሳሳይ የሆኑ ነገሮችን ነገር ግን በአካል ወይም በቁጥር የተለያዩ መሆናቸውን የሚገልጽ ቃል ነው።[4]ለምሳሌ፦ “በክርስቶስ ጸጋ እናንተን ከጠራችሁ ከእርሱ ወደ ልዩ ወንጌል( #ἕτερον εὐαγγέλιον) እንዲህ ፈጥናችሁ እንዴት እንዳለፋችሁ እደነቃለሁ፤” — ገላትያ 1፥6 ሔቴሮን ኢዋንጌሊዮን(ἕτερον εὐαγγέλιον) የሚለው ሐረግ በአይነቱም ሆነ በይዘቱ ለገላትያ ሰዎች ከተሰበከላቸው ከቀድሞው ከእውነተኛው እና ከቀጥተኛው ወንጌል ፍጹም ሌላ (ሔቴሮስ/ἕτερος) ወይም የተለየ መሆኑን የሚገልጽ ነው። “ስምዖን ጴጥሮስም ሌላውም ደቀ መዝሙር(አሎስ ማቴቴስ/ἄλλος μαθητής) ኢየሱስን ተከተሉ። ያም ደቀ መዝሙር በሊቀ ካህናቱ ዘንድ የታወቀ ነበረ፥ ወደ ሊቀ ካህናቱም ግቢ ከኢየሱስ ጋር ገባ፤”— ዮሐንስ 18፥15 በግሪኩ “አሎስ/ἄλλος” የሚለው ቃል ከስምዖን ጴጥሮስ የተለየ ማንነት እንዳለ ወይም በማንነታዊ መገለጫ ፈጽመው የተለያዩ አካላቶች እንደሆኑ የሚያሳይ ቃል ነው። ይህም ማለት ደግሞ ሁለት በአገልግሎታቸው፣ በምንነታዊ ባህሪዎታቸው(ሰው በመሆናቸው) እና የመጠሪያ ማዕረጋቸው አንድ አይነት የሆኑ ነገር ግን በአካል ሆነ በማንነታቸው ደግሞ የተለያዩ ሁለት ሰዎች መሆናቸውን ይገልጻል። የሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስን የጽሑፎቹን የሰዋሰው አወቃቀርና የቃላት አጠቃቀም በተመለከትን ጊዜ ምን ያክል ለቋንቋ ህግጋት ጥንቃቄዎችን እንደሚያደርግ እናስተውላለን። በዮሐ 14፥15-16 ላይ ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ ከእኛ ጋር ለዘላለም የሚኖረው አጽናኙ በአካል ከአብ እና ከወልድ የተለየ፤ በባህሪዎቱ እና በምንነቱ ደግሞ ከአብ እና ከወልድ ጋር ተስተካክሎተ ኑባሬ ያለው አካል መሆኑን ለመግለጽ “አሎስ/ἄλλος” የሚለው የጽርዕ (ግሪክ) ቃል እንደተጠቀመ እንመለከታለን። በተጨማሪም ቁጥር 17ን ስንመለከት፦ “ እርሱም(αὐτὸ) ዓለም የማያየውና የማያውቀው ስለ ሆነ ሊቀበለው የማይቻለው የእውነት መንፈስ ነው፤ ነገር ግን ከእናንተ ዘንድ ስለሚኖር በውሥጣችሁም ስለሚሆን እናንተ ታውቃላችሁ።”  — ዮሐንስ 14፥17 በዚህ ክፍል ላይ የእውነት መንፈስ(τὸ πνεῦμα τῆς ἀληθείας/ቶ ኒውማ ቴስ አሌቴያስ) የተባለው አካል እርሱ(αὐτὸ) ሊባል የሚችል ማንነታዊ ቅዋሜ ያለው አካል እንደሆነ በግልጽ ሁኔታ ያስረዳል።[5] በተጨማሪም “..ከእናንተ ዘንድ ስለሚኖር/ὅτι παρ’ ὑμῖν μένει…” በሚለው ሐረግ ውስጥ “ስለሚኖር” ማለትም በግሪኩ ሜኔይ/μένει በሚለው ግሳዊ ቃል በተባእታይ ጾታ የመጣ እርሱ/He የሚል ውስጠ ተውላጠ ስም እንዳለ እንመለከታለን። በተለያዩ የዮሐንስ ወንጌል ክፍሎች ላይ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መንፈስ ቅዱስን እርሱ እያለ በተባዕታይ ጾታ ሲጠራው እንመለከታለን። ይሄ ደግሞ የመንፈስ ቅዱስን አካላዊ ማንነት የሚያስረዳ ነው። መንፈስ ቅዱስ በኑባሬያዊ ማንነቱ በግዑዝ ጾታ አለመጥራቱ የራሱ የሆነ ማንነት እንዳለው አስረጂ እና አመላካች ነጥብ ነው።[6] ቀጥሎ በዮሐንስ ወንጌል ላይ መንፈስ ቅዱስ እርሱ እየተባለ በተባዕታይ ጾታ የተጠራባቸውን ክፍሎች እንመልከት፦ በዮሐንስ 14፥26 እና 15፥26 ላይ መንፈስ ቅዱስ በሶስተኛ መደብ ሰብአዊ ተውላጠ ስም ኤኬይኖስ/ἐκεῖνος “እርሱ” ተብሎ ተጠርቷል። በተጨማሪም አጽናኝ በግሪኩ ፓራክሌቶስ/παράκλητος የሚለው ስም በባለቤት ሙያ በተባዕታይ ጾታ የመጣ ስም ነው፦ “አብ በስሜ የሚልከው ግን መንፈስ ቅዱስ የሆነው አጽናኝ (ፓራክሌቶስ/παράκλητος) እርሱ (ኤኬይኖስ/ἐκεῖνος) ሁሉን ያስተምራችኋል እኔም የነገርኋችሁን ሁሉ ያሳስባችኋል።”  — ዮሐንስ 14፥26 “ዳሩ ግን እኔ ከአብ ዘንድ የምልክላችሁ አጽናኝ (ፓራክሌቶስ/παράκλητος) እርሱም ከአብ የሚወጣ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ፥ እርሱ (ኤኬይኖስ/ἐκεῖνος) ስለ እኔ ይመሰክራል፤”  — ዮሐንስ 15፥26 በተጨማሪም በዮሐንስ ወንጌል በምዕራፍ 16 ቁጥር 7 ላይ የሚላከው አካል “እርሱን” አውቶን/αὐτὸν በማለት በሶስተኛ መደብ ሰብአዊ አገናዛቢ ተውላጠ ስም ተባዕታይ ጾታ ሲጠራው እንመለከታለን፦ ⁷ እኔ ግን እውነት እነግራችኋለሁ፤ እኔ እንድሄድ ይሻላችኋል። እኔ ባልሄድ አጽናኙ ወደ እናንተ አይመጣምና፤ እኔ ብሄድ ግን እርሱን (አውቶን/αὐτὸν) እልክላችኋለሁ።… ¹³ ግን እርሱ ἐκεῖνος የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ወደ እውነት ሁሉ ይመራችኋል(ሆዴጌሴይ/ὁδηγήσει)፤ የሚሰማውን (አኩሴይ/ἀκούσει) ሁሉ ይናገራል (ላሌሴይ/λαλήσει) እንጂ ከራሱ (ሄአውቱ/ἑαυτοῦ) አይነግርምና፤ የሚመጣውንም ይነግራችኋል (አናንጌሌይ/ἀναγγελεῖ)።¹⁴ እርሱ (ኤኬይኖስ/ἐκεῖνος) ያከብረኛል፥ ለእኔ ካለኝ ወስዶλήμψεται ይነግራችኋልና።— ዮሐንስ 16፥7፣13፣14 በቁጥር 13 እና 14 ላይ ያሉት ግሶች ስንመለከት(ይመራችኋል፣ የሚሰማውን፣ ይናገራል፣ ይነግራችኋል …ወዘተ) “እርሱ” የሚል ተባዕታይ ውስጠ ተውላጠ ስም አለ። ይህ ሁሉ የሚያሳዩት ወይም አመላካች የሆኑት የመንፈስ ቅዱስን አካላዌ ህያውነት ወይም ኅልወትን እንደሆነ እንረዳለን። ስለዚህ መንፈስ ቅዱስ

ኃልወተ መንፈስ ቅዱስ Read More »

ዘላለማዊ ቃል ወልድ ከአብ በኑባሬው ያነሰ እና ለአብ የሚገዛ ነውን?

“…በዚያን ጊዜ ልጁ ራሱ ደግሞ ሁሉን ላስገዛለት ይገዛል።”1ኛ ቆሮንቶስ 15፥28 “…τότε καὶ αὐτὸς ὁ υἱὸς ὑποταγήσεται τῷ…”1Cor 15:28 ሃይፖታጌሴታይ/ὑποταγήσεται የሚለው ቃል ሃይፖታሶ/ὑποτάσσω ከሚለው ስርወ ቃል የመጣ ሲሆን መታዘዝ፣ መተናነስ ወይም ደግሞ መገዛትን የሚያመለክት ነው። አንዳንድ ሐያስያንና የክርስቶስን አምላክነት የሚክዱ(ሙስሊሞችንም ያጠቃልላል) መናፍቃን በ1 በቆሮንጦስ ምእራፍ 15 ላይ አብ ሁሉን ነገር ለወልድ ካስገዛለት በኋላ ወልድ ራሱ ደግሞ ሁሉን ላስገዛለት ለእርሱ እንደሚገዛ የሚናገረውን ክፍል በመጎንተል ክርስቶስ ኢየሱስ አምላክ አይደለም ለማለት ይዳዳቸዋል። መገዛት ወይም መተናነስ (subordination) የሚለው ቃል በምን አግባብና አገባብ እንደሚውል ከማየታችን በፊት ስለ ነባቤ እንሰተ ቃል (subordination view) በትንሹ እንመለከታለን። በSubordinationism ዙርያ እስከ 4 መቶ ክፍለ ዘመን አጋማሽ ብዙ ሀሳቦችንና አስተምህሮቶች ተሰንዝረውበታ። በዚህም ዙሪያ የሁለት ጎራዎችን ምድብ ነጥብ በነጥብ እንመልከት፦ አንደኛው፦ ሆሞዮስዮስ/ὁμοιούσιος ሆሞዮስዮስ የሚለው የግሪክ ቃል”ሆሞዮስ/ὅμοιος” “ተመሳሳይ” ወይም “ተቀራራቢ” ከሚለውና “ኡሲያ/οὐσία” “ኑባሬ” ወይም “ባህሪ” ከሚሉት ጥምር ቃላቶች የተገኘ ሲሆን ኢንግሊዘኛው ontological subordination ሲለው የአማርኛው የቁም ፍቺው ደግሞ “ኑባሬያዊ እንሰት” ወይም “በባህሪ መተናነስን” ያመላክታል። በዚህ መርሆተ ቃል በነገረ ክርስቶስ(christology) ዙሪያ ብዙ የኑፋቄ ትምህርቶች ተነስተዋል። ከእነዚህም መካከል እውቁ የኑፋቄ መምህር የአሌክሳንድሪያው ጳጳስ አርዮስ ከክርስትናውና ከቅዱሱ መጽሐፍ ያፈነገጠ አስተምህሮ በመለኮታዊ በኑባሬ ወይም በባህሪ አንጻር ያለን መተናነስን ወይም መበላለጥን (ontological subordination) አስተማረ። በአሁኑ ጊዜ ለተነሱት የኑፋቄ ትምህርቶች ለጅሖቫ ምስክሮች ለኢብዮኒዝም(Ebionism) አስተምህሮ እንደውም ለመሐመዳውያን ለእስልምና መነሳሳት ትልቅ ጠባሳ ጭሮ ያለፈ እንደሆነ ይገመታል። ሁለተኛው፦ ሆሙስዮስ/ὁμοούσιος ሆሙስዮስ ማለት “ኡሲያ/οὐσία” “በኑባሬ” ወይም “በባህሪ” አንድ አይነት ወይም እኩል መሆንን ያሳያል። በ325 አ.ም በኒቂያው ጉባኤ ላይ በተደረገው ጉባኤ የአርዮስን የተሳሳተ የሰቦርዲኔሽናል ፈርጅ ማለትም የወልድን ለአባቱ መገዛቱ  ontological subordination ወይም “ኑባሬያዊ እንሰት” በማውገዝ የክርስቶስ ለአባቱ መገዛቱ ግብራዊ እንሰት/functional subordination ያመላክታል በማለት ወልድ ከአብ ጋር በባህርዮቱና በኑባሬው ከአባቱ ጋር እኩል ወይም አንድ አይነት (ሆሙስዮን ቶ ፓትሪ/ὁμοούσιον τῷ Πατρί) መሆኑን ገልጸውልናል። በመጨረሻም ወልድ ለአባቱ መገዛቱ፤ መታዘዙ እና ያባቱን ፈቃድ ማገልገሉ በአባትና በልጅ መካከል ያለውን የማንነትና በባህሪም ሆነ በኑባሬ መተናነስን ሆነ መበላለጥን ፈጽሞ አያመለክትም። ቅዱስ ባስልዮስ በክታቡ፦ “…አብ ከወልድ ከመንፈስ ቅዱስ ተለይቶ አንዲት ሰዓት እንደ ዓይን ጥቅሻ ያህል ስንኳ አልነበረም ሁል ጊዜ ከነርሱ ጋር የነበረ የሚኖር ነው እንጂ።…”[1] በማለት በሥላሴ መካከል አንዳች ብልጫ ወይ መተናነስ እንደሌለ ይሄ አባት ያስቀምጠዋል። የቆሮንቶስን መጽሐፍ ለመረዳት ከቅዱሳት መጽሐፍት ምሳሌ እንጠቀም። በሉቃስ ወንጌል ምእራፍ 2 በቁጥር 51 ላይ ጌታችን ክርስቶስ ኢየሱስ በናዝሬት ከተማ ለቤተሰቡ ይታዘዛቸው እንደ ነበር ቅዱስ ቃሉ ይነግረናል። በዚህ ክፍል ላይ ይታዘዝላቸዋል የሚለው የግሪክ ቃል ከ1ኛ ቆሮንቶስ 15፥28 ወልድ ለአባቱ እንደሚገዛ በሚናገረው ክፍል ጋር ተመሳሳይ ቃልን ነው የተጠቀመው፦ (ሃይፖታሶ/ὑποτάσσω) “ከእነርሱም ጋር ወርዶ ወደ ናዝሬት መጣ፥ ይታዘዝላቸውም (ὑποτασσόμενος) ነበር። እናቱም ይህን ነገር ሁሉ በልብዋ ትጠብቀው ነበር።” ሉቃስ 2፥51 ከዚህም የምንረዳው ክርስቶስ ኢየሱስ ለቤተሰቡ ሲታዘዝ ከእነርሱ በማንነት፤ በባህሪዎትና በኑባሬ ተናንሶ ወይም ዝቅ ማለቱን ሳይሆን በልጅና በወላጅ መካከል ያለውን መታዘዝ ወይም የመከባበር መስተጋብር በሚያሳይ ረገድ መሆኑ እውቅና ቅቡል ነው። በሌላ በኩል ደግሞ በኤፌሶን ምእራፍ 5 በቁጥር 21-22 ሐዋርያው ጳውሎስ “…ለባሎቻችሁ ተገዙ(ሃይፖታሶ/ὑποτάσσω)…”  ብሎ ሲል ሴቶች ከወንዶች እንደሚያንሱ እየገለፀ እንዳልሆነ ለገላትያ የጻፈውን መልእክት በምእራፍ 3 በቁጥር 28 ላይ ባለው በቀላሉ እንረዳለን፦ “አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም፥ ባሪያ ወይም ጨዋ ሰው የለም፥ ወንድም ሴትም የለም፤ ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁና።”— ገላትያ 3፥28 በሴትና በወንድ መካከል ያለው መተናነስ ኑባሬያዊ(ontological) ሳይሆን ግብራዊ መተናነስን(functional subordination) ነው የሚያመለክተው። ስለዚህ በቆሮንቶስ 15፥28 ጥቅስ መሠረት ወልድ ከአብ ያንሳል ማለት በፍፁም አይቻልም ማለት ነው። ጸጋ ሰላም ይብዛላችሁ። ዋቢ ምንጭ 1] ሐይማኖት አበው ምዕራፍ ፴፫ ክፍል ፭

ዘላለማዊ ቃል ወልድ ከአብ በኑባሬው ያነሰ እና ለአብ የሚገዛ ነውን? Read More »

ማቴዎስ 28፥19 እና ሰዋሰዋዊ ሙግት

በማቴዎስ 28:19 በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም የሚለው ሐረግ የአካል ሦስትነትን አያሳይም የሚሉ መናፍቃን ሙግት የሚንድ ሆኖ የሚቀጥ ነው። ምክንያቱም ከስም ባሻገር የአካላዊ ሶስትነትን ያሳያል። በአንደኛው መቶ ክፍለ ዘመን ውስጥ እንደተጻፈ የሚታመነው ዲዳኬ (ትምህርተ ሐዋርያት) ጽሑፍ ላይ ስለ ጥምቀት ስርአት በማቴዎስ ወንጌል ላይ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያስተላለፈውን ትእዛዝና ሐዋርያት በዛ ዘመን እንዴት እንደሚያጠምቁ ሲያብራራ እንመለከታለን፦ “…ስለ ጥምቀትም ረገድ እንዲህ አጥምቁ፤ ይህን ሁሉ በመጀመሪያ ከተናገርክ በኋላ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም በሕያው ውኃ አጠምቁ (“…βαπτίσατε εἰς τὸ ὄνομα τοῦ πατρὸς καὶ τοῦ υἱοῦ καὶ τοῦ ἁγίου πνεύματος…”)…….በአብ፣ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም ራስ ላይ ሦስት ጊዜ ውኃ አፍስሱ…” [ትምህርተ ሐዋርያት ስለ ጥምቀት ህግጋት][1] አንዳንድ ጸረ ስላሴያውያን የማቴዎስ ወንጌል 28:19 የስላሴን አስተምህሮ አያሳይም በማለት ክፉኛ ሲሞግቱ እንመለከታለን። ነገር ግን ይሄ አካሄዳቸው የበኩረ ጽሑፋቱን ቋንቋ ያማከለ ሙግት ፈጽሞ አይደለም። ይሄም የሚያሳየው የሰዋሰው ሙግት ላይ ምን ያህል ደካማ መሆናቸውን ነው። ይባሱን ብሎ ጽሑፉ በጥንታውያን ክታባት ላይ አይገኙም የሚሉም መጥተዋል። ለዛሬ እኛ በማቴዎስ ወንጌል 28:19 ያለው ጽሑፍ ላይ እናተኩር። ጥንታዊ ሰነድ የሆነው ዲዳኬ (ትምህርተ ሐዋርያት) የጥምቀት ስርዓትን በተመለከተ የአብ የወልድና የመንፈስ ቅዱስ ስም ከመጠቀሱም ባሻገር አካላዊ ልዩነቶች (Personal Distinction) እንዳላቸው በግልጽ ያሳያል። ይህም ማለት አብ፣ ወልድና መንፈስ ቅዱስ እያንዳንዱ አካል እኔነት እንዳለው የሚያሳይ ክፍል ነው። የክፍሉን የሰዋሰው መዋቅር ከመመልከታችን በፊት አንድ ወሳኝ ህግ እንመልከት፦ በ1735-1813 ይኖር የነበረው የግሪክ ቋንቋ ሊቅ እንዲሁም ባለ ብዙ ዘርፈ ሙያ ባለቤት የሆነው ግራንቪል ሻርፕ ስለ ውስን መስተኣምር አገባብ እና የአረፍተ ነገሩን አተረጓጎም ሒደት ላይ ባስቀመጠው ስድስት ህጎች መካከል በስድስተኛው ነጥብ ላይ እንዲህ የሚል መርህ እናገኛለን፦ “ሁለት ወይም ከዛ በላይ ተመሳሳይ ሙያ(case) ያላቸው ስሞች(የማዕረግ )፤ በ ‘እና/ካይ (καὶ)’ ተያይዘው፤ በስሞቹ መጀመሪያ ላይ ውስን መስተኣምር ካለ አረፍተ ነገሩ ስለ ተለያየ አካል(person) የሚናገር ነው”[2] “πορευθέντες οὖν μαθητεύσατε πάντα τὰ ἔθνη, βαπτίζοντες αὐτοὺς εἰς τὸ ὄνομα τοῦ πατρὸς καὶ τοῦ υἱοῦ καὶ τοῦ ἁγίου πνεύματος”[Κατα Μαθθαιον 28:19] በዚህ ህግ መሰረት የማቴዎስ ወንጌል 28፥19 ያለው ክፍል ይሄንኑ ህግ አሟልቶ እንመለከታለን። አብ፣ ወልድ፣ መንፈስ ቅዱስ የሚሉት የማዕረግ ስሞች ተመሳሳይ ሙያ ያላቸው ነጠላ ስሞች(የቃል ክፍሉ Noun, የሙያ መደቡ Genitive case, የብዜት ቁጥሩ Singular) ስለሆኑ አብ፣ ወልድና መንፈስ ቅዱስ የተለያዩ ማንነቶች እንደሆኑና ያልተጨፈለቁ አካላቶች መጠቀሳቸው በግልጽ ህጉ ይደግፍልናል። ይህ ደግሞ ስም ብቻ መጠቀሱን አይተን በቀላሉ እንድናልፍ የሰዋሰው ውቅረ ህጉ አይፈቅድልንም። በዚህም መስፈርት ከሄድን ከማቴዎስ ወንጌል በተጨማሪ በ2ኛ ቆሮንቶስ ም.13 ቁ.14 የሰዋሰው አወቃቀሩ ተመሳሳይ ነው የህጉን መስፈርት ያሟላል። ጸጋ ሰላም ይብዛላችሁ! ዋቢ ምንጮች

ማቴዎስ 28፥19 እና ሰዋሰዋዊ ሙግት Read More »

ቅድመ ኒቂያ አበው ትምህርተ ሥላሴ እና የቤተ ክርስቲያን ታሪክ

ሰላም እንደምን ቆያችሁን በባለፈው ልጥፍ ማለትም በመጽሐፍ ዳሰሳችን የትምህርተ ሥላሴ ቀዳማይ አመንጪ ጉባኤ ኒቂያ አለመሆኑን በአጭሩም ቢሆንም አይተናል። ይህ አይነት አስተሳሰብ ላላቸው(ቅድመ ኒቂያ ጉባኤ ያሉት የቤተ ክርስቲያን አበው ሥላሴን  የሚገልጽ ነገር ፈጽሞ አላስተማሩም) ለሚሉት ትችት ታሪክን ካለማንበብ የመነጨ እንደሆነ እናስተውላለን። ይህንን ማሳያ ከሌሎች አበው አንጻር በማቅረብ እንዘልቃለን። የቤተ ክርስቲያን አበው ስለ ሥላሴ የነበራቸውን መረዳት እዚህ ጋር አምጥቶ መጻፍ እጅጉን ብዙ ነው። ከእነዚህም መካከል ጥቂቱን እናጋራችሁ፦ 1)Clement of the Rome(30-95) ቅዱስ ቀለሜንጦስ የሐዋርያውን ቅዱስ ጳውሎስን ኤፌሶን ላሉት ምእመናን በጻፈው መልእክት ላይ በምዕራፍ 4 ከቁጥር 4 እስከ 6 ባለው ሐሳብ ተሞርክዞ የስላሴን አንድነትና ሶስትነት ሲገልጽ እንመለከተዋለን፦ “….አንድ አምላክ፤ አንድ ክርስቶስ፣ በእኛ ላይ የፈሰሰው አንድስ የጸጋው መንፈስ ያለን አይደለንምን? [1] ኤፌሶን 4፥4-6″…⁴ በመጠራታችሁ በአንድ ተስፋ እንደ ተጠራችሁ አንድ አካልና አንድ መንፈስ አለ፤ ⁵ አንድ ጌታ አንድ ሃይማኖት አንዲት ጥምቀት፤ ⁶ ከሁሉ በላይ የሚሆን በሁሉም የሚሠራ በሁሉም የሚኖር አንድ አምላክ የሁሉም አባት አለ።(——ኤፌሶን 4፥4-6) 2)Hippolytus of Rome(3rd ce. earlier)፦ በ3ኛው መቶ ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ላይ የሮሙ ሂፖሊተስ ኖተስ(Noetus) ለተባለ የሰምርኔስ ክርስቲያን(Christian from Smyrna) ሂፖሊተስ ምንፍቅና ነው ብሎ ያመነበትን የፓትሪፓሻውያንን አመለካከት ሲያራምድ ለነበረው መናፍቅ ምላሽ በኖተስ ላይ የጻፈው ጽሑፍ ስለ አስተምህሮተ ስላሴ እንዲህ ብሎ ሲሞግት እንመለከታለን፦ “…እንግዲህ የአብን መስተጋብራዊ ግንኙነትን፤ ፈቃዱንና አብም ከዚህ መንገድ ውጭ ሊመለክ እንደማይፈልግ አውቆ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀመዛሙርቱ ይሄንን ትእዛዝ ሰጣቸው፦’እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው፥ ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው…'(— ማቴዎስ 28፥19-20) ከእነዚህም አንዱን ያጎደለ ሰው እግዚአብሔርን ፍጹም በሆነ መንገድ እንዳላከበረ ጭምር አሳይቶናል። ምክንያቱም እግዚአብሔር የሚከብረው በስላሴ በኩል ነው። አብ ፈቅዷልና ወልድ አደረገ መንፈስ ቅዱስም ተገለጠ ይቺም የአብ ቃል ናትና…”[2] 3) ጠርጡሊያኖስ ወይም ተርቱሊያኖስ (Tertullian 160-215) ፦ የጥንቷ የቤተ ክርስቲያን አባት የሆነው ጠርጡሊያኖስ በስላሴያዊ አስተምህሮት ላይ ለሚነሱ ኑፋቄዎች መልስ በመስጠትና ቤተክርስቲያን እምነት ላይ ከሚሰሩ አቃብያነ አባቶች መካከል አንዱ ነው። ለምሳሌ በመናፍቃን ሙግት ላይ ባነሳው በፕራክሲየስ (against praxeas) ለሞዳሊስት አራማጅ የሆነው የፓትሪፓሺያን(Patripassian) ሐሳብ አንስቶ እንዲህ ሲል በሙግቱ ላይ ጽፏል፡- “…ሶስቱ አብ፣ ወልድና መንፈሱ ናቸው። ሶስት ናቸው ነገር ግን በሁናቴ አይደለም በግብር እንጂ፤ በኑባሬም አይደለም በአካል እንጂ፤ በስልጣን ወይም በሐይል አይደለም በአይነት እንጂ ሆኖም ግን እግዚአብሔር አምላክ አንድ ኑባሬ፣ ስልጣን፣ ሐይል አለው ምክንያቱም በአካል፣ በግብርና በአይነት በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ የተገለጠ አንድ አምላክ ነውና…”[3] 4)አርጌንስ (Origen 185-254) ፦ አርጌንስ የተባለው አባት ከጠርጡሊያኖስ ትምህርት በመነሳት ከእርሱ ጋር በተመሳሰለ ሁኔታ ስለ አስተምህሮተ ስላሴን ሲደግፍ እንመለከታለን። ነገር ግን አርጌንስ በስላሴ አካላት መካከል እንደ ጠርጡልያኖስ በደረጃ (ወይም በsubordination) ረገድ ልዩነት መኖሩን እንደሚያምን ከጽሑፋቱ እንመለከታለን። ሆኖም ግን ኦሪገን የጻፈው የመጀመሪያው መርህ (De Principiis or Peri Archon) እጅግ ጥንታዊ የሆነ የስነ መለኮት ትምህርት ግኝት እንደሆነ ሊቃውንት ያትታሉ። በጽሑፉም ላይ በስላሴ ማመን እንዴት አስፈላጊ እንደሆነ አትቶልን እናገኛለን፦ “…ስላሴ ዘላለማዊ ነው……….በእርግጥ ከስላሴ ውጭ ያሉ ነገሮች ሁሉ በጊዜና በእድሜ ሊለኩ ይችላሉ። ደግሞም ማንም ሰው ለመዳን ወይም “እንደገና ከእግዚአብሔር ለመወለድ” አብ፣ ወልድና መንፈስ ቅዱስ እንደሚያስፈልገውና ከሥላሴ እምነት ውጪ ደህነትን የማያገኝበትን እንዲሁም ያለ መንፈስ ቅዱስ የአብ ወይም የወልድ ተካፋይ መሆንን የማይችልበትን ምክንያት ለምን እንደሆነ መጠየቁ ተገቢ ይመስለኛል። በእነዚህ ነጥቦች ላይ በመወያየት ለመንፈስ ቅዱስ፣ ለአብ እና ለወልድ ልዩ የሆነውን ተግባር(አስተምህሮ) መግለጽ እንደሚያስፈልግ አያጠራጥርም።”[4] 5)Gregory Thaumaturgus-Wonder worker/ጎርጎርዮስ ገባሬ ተአምራት ወመንክራት/(205–270)፦ “ሁሉም(አካላቶች) አንድ ምንነት፤ አንድ ባህሪዎት እና አንድ ፈቃድ አላቸው። ይህ ደግሞ “ቅድስት ስላሴ” ተብሎ ይጠራል። እንዲሁም እግዚአብሔር በንዑሳን ስሞች፣ በአንድ ምንነት ሶስት አካላት እና በአንድ አይነት ዘር (አካላቶቹ በባህሪ ደረጃ) የተገለጠ አምላክ ነው።”[5] ይሄን ካየን ከሁሉ በፊት የሌለ በኒቂያ ነው የሥላሴ ትምህርት የተጀመረው የሚልን ነገር በፍፁም እንደሙግት አንድም ሰው በክርስቲያኖች ላይ ሊያቀርብ በፍፁም አይችልም ማለት ነው። ሌሎች ተጨማሪ የቤተክርስቲያን አበው ላይ የሚነሳውን ተቃውሞ በባለፈው ልጥፋችን ጠርጡሊያኖስ በመቀጠል እንደምናስቀምጥ ነግረናችሁ ነበር። የሌሎቹንም አባቶች በክፍል በክፍል አደራጅተን የምናቀርብ ይሆናል። ጸጋ ሰላም ከሁላችን ጋር ይሁን ማጣቀሻ 1] /1Clement 46:6/ 2] /—Against Noetus Ch. 14./ 3] /Against Paraxeas 2/ 4] /De Principiis, book 1, chapter 3The Trinity according to Origen/ 5] Gregory Thaumaturgus, On the Trinity. ANF, VI:48

ቅድመ ኒቂያ አበው ትምህርተ ሥላሴ እና የቤተ ክርስቲያን ታሪክ Read More »

ትምህርተ ሥላሴ እና የቤተክርስቲያን ታሪክ

የመጽሐፍ ዳሰሳ [1] በመጀመሪያ ይህን ክፍል ለማጥናት ምሥጢረ ስላሴ ምን ማለት ነው!? የትምህርተ ሥላሴ ቀዳማይ አመንጪ መጽሐፍ ቅዱስ ነው። አንዳንድ ሥላሴን ስሩን ሳይዙት አውቀን ጨርሰናል በማለት ሲናገሩ አስተውያለሁ በዕውነቱ ያሳዝናል ለዚህም ነው በተለይ በአባቶች መምህራን የምሥጢረ ሥላሴ   በስፋቱና በትልቅነቱ ሲነገርም እንዲህ ይባላል፦ “..ምሥጢረ ሥላሴን ጠልቆ ለማወቅ መሞከር ባሕረ ውቅያኖስን በዕንቁላል  እየቀዱ ለመጨረስ እየጨለፉም ለመጨለጥ እንደ ማሰብ ነው ይላሉ…” እውነት ነው፤ ለሰው ከተሰጡ ስራዎች ምሥጥረ ሥላሴን ከመመርመር የሰፋና እና የከበደ የለም። ➝ ሆኖም ስለ ሥላሴ በትክክል ማሰብ ለክርስቲያናዊ ኑሮ ዋንኛ ነገር መሆኑን አንባቢ ልብ ይበል። አይሁድ፣ ክርስቲያኖችና ሙስሊሞች አንድን አምላክ ሲያመልኩ፥ የሥላሴን ትምህርት በአንድ አምላክ ከሚያምኑ ሌሎች ሁሉ ክርስቲያኖች ይለዩዋቸዋል። ስለዚህ ክርስቲያን ለራሱ ብቻ ሳይሆን የራሱን እምነት ለሌሎች ለመግለጥም የሥላሴን ትምህርት ማወቅ ይገባዋል። ➝ሥላሴ የሚለው ቃል በመጽሐፍ ቅዱስአይገኝም። በግእዝ ቋንቋ ቃሉ ሦስትነት ማለት ነውና በትምህርተ መለኮት ጥቅም ላይ ሲውል..በአንዱ እግዚአብሔር ሦስት አካላት እንዳሉ ያሳስባል። በ2ኛው መቶ ዓመት የአንጾኪያ ጳጳስ የነበረው ቴዎፍሎስ በግሪክ ቋንቋ ትሪአስ እና ጠርጡሊያን በላቲን ቋንቋ ትርንታስ በእንግሊዘኛው ደግሞ TRINITY የሚለው ሲሆን፣ ቃሉ “Tri” ወይም “ሦስት” እና “Unity” ወይም “ኅብረት/አንድነት” ከሚሉት ሁለት የላቲን ቃላቶች የመጣና አንድ ቃል ሆኖ በተገናኝ የሚነበብ (“tri” + “unity” ) ነው። ሥላሴ የሚለው ቃልና ትምህርቱ እንደ መነጥር ሆነው በመፅሐፍ ቅዱስ ያለውን ትምህርት ጉልሕ ሆኖ እንዲታየን ያደርጋሉ እንጂ በእግዚአብሔር ቃል ላይ አዲስን ትምህርት አይጨምሩም። ትምህርተ ሥላሴ ለክርስቲያን ረቂቅ ፍልስፍናም አይደለም። ወደፊት እግዚአብሔር ቢፈቅድ ሥላሴን በደንብ እንመረምራለን። ወደ ዋናው ርዕሳችን ወደ ሚያንደረድር ሀሳብ ስንመለስ፦ ትምህርተ ሥላሴ እንደ አርዮስ ያሉ የመናፍቃን ጥቃት በቤተክርስቲያን ላይ ሲያደርሱ የመጠበቁ ሂደት ውስጥ ትልቅ ድርሻ ከነበራቸው አትናቴዎስ(Athanasius) አንዱ ቢሆንም ርእሰ ጉዳዩን በዳበረ መልኩ የተነተኑት ቀጰዶቃውያን አበው ናቸው። በመጀመሪያ ከዛ በፊት ቀጰዶቃውያን አበው እነማን ናቸው የሚለውን በጥቂቱ እንመልከት… ቀጰዶቃውያን አበው(Cappadocian Fathers) የሚባሉት ውስጥ፦ ትምህርተ ሥላሴ በቤተክርስቲያን ታሪክ ቅድመ ጉባኤ ኒቂያ አበው ግንዛቤአቸው ምን ነበር? ከላይ እንዳየነው ሥላሴ የሚለው ቃል በአዲስ ኪዳን ባይገኝም ትምህርተ ሥላሴ የነገረ መለኮት ዐብይ ርዕስ መሆኑን አይተናል። የአዲስ ኪዳን ጸሐፊዎች ምን ያህል ትምህርተ ሥላሴን እንደተረዱት ባናውቅም ግን፥ እግዚአብሔር ሦስት አካላት እንዳሉ አምነው የመለኮትን አንድነትንና የአካል ሦስትነትን ለትምህርታቸው መሠረት አደረጓቸው። የትምሕርተ ሥላሴ ቀዳሚ አመንጪ መጽሐፍ ቅዱስ ቢሆንም፣ በሐዋሪያት እግር ስር የተማሩ ቀደምት የሆኑ የቤተክርስቲያን አበው ምን አሉ የሚለውን ጉዳይ መቃኘት፣ የተዛባ የታሪክ መረጃ ያላቸው ሰዎችን ለማቅናት ጠቃሚነት ስላለው ይህ ጽሑፍ ዳሰሳዊ ጥናት ስለሆነ የሁሉንም አበው እማኝነትና ትምህርት በክፍል አንድ በስፋት ማቅረብ ስለማይቻል በተወሰነው እንመለከታለን። 1) ጶሊቃርጶስ (Polycarp) :- በ70ዓ.ም ተወልዶ በ155 ዓ.ም ወይም በ160 ዓ.ም የሞተ፣ የሐዋሪያው ዮሐንስ ደቀ መዝሙር የነበረ እንዲሁም የሰምርኔስ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳሳት የነበረ ሰው ነው።..ይህ ሰው ትምህርተ ሥላሴን በተመለከተ እንዲህ ብሏል፦ “ሁሉን ቻይ እግዚአብሔር ሆይ…ዘላለማዊና ሰማያዊ በሆነ ሊቀ ካህናት በምትወደውና ባከበርኸው ልጅህ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ለአንተና ለእርሱም እንዲሁም ለመንፈስ ቅዱስ አሁንም ሆነ ለዘላለም ክብር ይሁን”[2] 2) ዮስጦስ ሰማዕት (Justin Martyr) ፦ የቤተክርስቲያን አቃቤ እምነት የነበረና የሰማዕትነትን ክብር የተቀናጀው ይህ አባት አባት በ100 ዓ.ም ተወልዶ በ165 ዓ.ም እንደ ሞተ ይገመታል። ይህ አባት ትምህርተ ሥላሴን በተመለከተ እንዲህ ብሏል፦ “የዓለማት ጌታ በሆነው በእግዚአብሔር በስመ አብ፣ በመድሐኒታችንም ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲሁም በመንፈስ ቅዱስ በውሃ መታጠብን ያገኛሉ”[3] 3)አግናጢዮስ ዘአንጾኪያ (Ignatius of Antioch) ፦ የአንጾኪያ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳሳት የነበረና በ98 ዓ.ም ወይም በ117 ዓ.ም እንደሞተ የሚገመት ክርስትናን ከመናፍቃን በመከላከሉ ዙሪያ ብዙ የጻፈ ዐቃቤ ክርስትና ነው። እንዲህም አለ፦ “በእምነትና በፍቅር፤ በወልድ፣ በአብና በመንፈስ ቅዱስ፤ በመጀመሪያው እና በመጨረሻው፤ ከሚያስደንቅ ጳጳስችሁ ጋር እናም እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ካሉ ዲያቆናት ጋር በሚገባ በጠበቀ መንፈሳዊ አክሊል የምታደርጉትን ሁሉ በስጋና በመንፈስ እንዲከናወን በጌታችንና በሐዋርያት ትምህረት እድትጸኑ አጥኑ። ክርስቶስ ኢየሱስ ለአብ በስጋው እንደተገዛለት እናም ሐዋርያት ለክርስቶስ፣ ለአብና ለመንፈስ ቅዱስ እደሚታዘዙ እናንተም ለጳጳሳችሁ እና እርስ በእርሳችሁ ተገዙ(ታዘዙ) በዚያን ጊዜ በስጋችሁም በመንፈሳችሁም አንድነት ይኖራችኋል።”[4] 4) ጠርጡሊያኖስ ወይም ተርቱሊያኖስ (Tertullian 160-215) ፦ አፍሪካዊ ዕቃቤ ክርስትና እንዲሁም የነገረ መለኮት ሊቅ ነው። ክርስትናን ከመናፍቃንና ከሌሎች ሐያስያን ለመከላከል ብዙ ጽፎአል፦ “አብና ወልድ ሁለት ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ደግሞ ሦስት መሆናቸውን እንገልጻለን። የቁጥሩንም ቅድመ ተከተል ከድነት አንጻር ነው….ይህም አንድነትና ሦስትነትን መሠረት አድርጎ ሦስቱንም ማዕከል ያደረገ ነው፤ እነርሱም አብ፣ ወልድና መንፈስ ቅዱስ። [አብ፣ ወልድና መንፈስ ቅዱስ] ሦስት ናቸው….ነገር ግን በባሕርይ ሳይሆን በገጽ፣ በኀይል ሳይሆን ነገር ግን በዐይነት። በባሕርይና (Substance) በኀይል አንድ ናቸው፤ ምክንያቱም አንድ አምላክ ብቻ ስላለና ይህም ባሕርይ፣ ገጽና ዐይነት በአብ፣ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ዙሪያ ያለ በመሆኑ”[5] 5) አርጌንስ (Origen 185-254) ፦ የእስክንድርያ ቤተ ክርስቲያን የነገረ መለኮት ምሁር ነው። አርጌንስ ክርስትናን በተመለከተ ብዙ የጻፈ ነው፦ “የእግዚአብሔር ቃል ወይም የእግዚአብሔር ጥበብ ጅማሬ አለው የሚል ማንኛውም ሰው፣ ቢያንስ እግዚአብሔርን መናቁ እንደሆነ ልብ ሊለው ይገባል…ምክንያቱም እግዚአብሔር ባለፉት ዓመታት ሆነ ዘመናት ከዚህ ውጪ ሊገመት በሚችልበት ጊዜ ሁሉ፣ እግዚአብሔር የጥበብ ባለቤት ነውና ይህ እውነት ለእግዚአብሔር አብ እንደሆነው ሁሉ ለወልድም ነው”[6] “እውነታው ይህ ከሆነ [መንፈስ ቅዱስ አሁን እንደ ሆነው ሁሉ ዘላለማዊ ካልሆነ፣ በዘመናት ውስጥ ዕውቀትን ገብይቶ መንፈስ ቅዱስን መሆን ከቻለ] መንፈስ ቅዱስ ለዘላለም ዓለም መንፈስ ቅዱስ መሆን ካልቻለ፣ እንደማይለወጠው አብና እንደ ልጁ ሁሉ መንፈስ ቅዱስ የሥላሴ አንዱ አካል ነው ማለት አይቻልም”[7] “የመለኮት ምንጭ ብቻ ሁሉን ነገር በቃሉና በምክንዩው የሚይዝ ከሆነ፣ በሥላሴ አካላት ውስጥ መበላለጥ ወይም መተናነስ የለም”[8] ሔሬኔዎስ(Irenaeus)፦ በ115 ዓ.ም ተወልዶ 190 ዓ.ም ሞተ፣ በልጅነቱ የሐዋርያው ዩሐንስ ደቀ መዝሙር ከነበረው ከጶሊቃርጶስ እግር ሥር የተማረ እንዲሁም የልዮን ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳሳት የነበረ ሰው ነው፦ “ቤተ ክርስቲያን በዓለም ሁሉ እንዲሁም እስከ ዓለም ዳርቻ ድረስ ብትበተንም፣ ቤተ ክርስቲያን ከሐዋርያትና ከእነርሱ ደቀ መዛሙርት የተቀበለችውን የሚከተለውን መሠረተ እምነት ነው፦…..ሁሉን ቻይ የሆነ እና ሰማይንና ምድርን እንዲሁም ባሕርን በእነዚህም ውስጥ የሚኖሩትን ሁሉ የፈጠረ አንድ እግዚአብሔር፤ በእግዚአብሔር ልጅ በአንዱ በኢየሱስ ክርስቶስ፣ ለድነታችን ሲል ትስብእት የሆነ፣ በመንፈስ ቅዱስ፣ የእግዚአብሔርን ዘመን በነብያቱ ያበሠረ እንዲሁም የተወዳጁ ጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ምጽአት፣ ከድንግል መወለድ፣ ሕማም፣ ከሙታን መነሣት፣ በአካለ ሥጋ ወደ ሰማይ ማረግ፣ “ሁሉን አንድ አድርጎ ለመሰብሰብ በአብ ክብር ከሰማይ መገለጥ፣ የሰው ልጆችን ሁሉ በአዲስ አካል ከሙታን ማስነሳት፣ ይኸውም ክርስቶስ ኢየሱስ ጌታችንና አምላካችን እንዲሁም አዳኛችንና ንጉሣችን መሆኑን፣ በማይታየው አብ ፈቃድ “በሰማይና በምድር ከምድርም በታች” ያለ ጉልበት ሁሉ እንዲበረከክለት፣ ምላስም ሁሉ ኀጢአት ብሎ እንደ ተሰዋ እንዲመሰክርለት ነው…”[9] ከጉባኤ ኒቂያ በፊት እንዲህ አይነት እምነት ያላቸው ከሆነ፣ የአስተምሮው ቀዳማይ አመንጪ ጉባኤ ኒቂያ ነው የሚባል ነገር ፈፅሞ የለም። ከሁሉ በፊት የሌለ በኒቂያ ነው የሥላሴ ትምህርት የተጀመረው ቢባል እንኳን ክርስቲያኑ ማህበረሰብ ከቀድሞው አስተምሮው ጋር የማይጣጣም ነው በሚል ተቃውሞ ለምን አላቀረበም? ለምንስ አላወገዘም? ኖሮስ ካለ ለምን በታሪክ ተዘግቦ አልተገኘም!? እነዚህን ከዚህ መጽሐፍ ዳሰሳ ካየን በተጨማሪ ጥናት ደግሞ በክፍል ሁለት ተመሳሳይ ሙግት አንስተን በጠርጡልያኖስ ላይ የሚነሱትን ሙግቶች የምንዳስስ ይሆናል። ማጣቀሻ 1] ትምህርተ ሥላሴ መሠረታውያን በዶ/ር ተስፋዬ ሮበሌ 2] Martyrdom of Polycarp, 14. ANF, I:42. 3] Justin, First Apology, LXI. ANF, I:183. 4] Epistle to the Magnesians, Chapter 13 5] Tertullian, Against Praxeas, 2. PL 2.156–57.፣ በቅንፍ ያለውን አይጨምርም። 6] De Princ. 1.2.; PG 11.132). 7] Alexander Roberts and James Donaldson, eds., The Ante-Nicene Fathers, Grand

ትምህርተ ሥላሴ እና የቤተክርስቲያን ታሪክ Read More »

አስተምህሮተ ሥላሴ አሕዳዊ ወይስ መድብላዊ?

“እስራኤል ሆይ፥ ስማ፤ አምላካችን እግዚአብሔር  አንድ_እግዚአብሔር ነው፤”  — ዘዳግም 6፥4 ሞኖቴይዝም(monotheism) የሚለው ግሪክ(ጽርዕ) ቃል ከሁለት ቃላት የተዋቀረ ሲሆን ሞኖስ(μόνος) ማለት አንድ ወይም ብቸኛ ማለት ሲሆን ቴዎስ(θεός) ማለት ደግሞ አምላክ ማለት ነው። በአጠቃላይ በስነመለኮት አንጻር አሐዳዊ አስተምህሮት የሚያንጸባርቅ አመለካከት ሞኖቴይዝም (monotheism) ይባላል። ከዚህ በተቃራኒው ደግሞ የመድብለ አማልክት አራማጆች ፖሊቴይዝም(Polytheism) ይባላሉ። ፖሉ(πολύ) ወይም ፖሊ ማለት ብዙ ማለት ነው። ከመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በፖሊቴይዝም ረገድ የሚታወቁ አገራት መካከል ሮማውያንና ግሪካውያን ግምባር ቀደም ነበሩ። ግሪካውያን ለብዙ ነገር አምላክ አላቸው። ለፍቅር፣ ለሰላም፣ ለቀን፣ ለጦር፣ ለወቅቶች፣ ለእድል….ወዘተ ለእያንዳዱ ተግባር አማልክት ነበሯቸው። ከሁሉም በላይ ደግሞ በጣም የሚገርመው የሚያመልኩት ነገር ከመብዛቱ የተነሳ ለማይታወቅ አምላክ በግሪኩ አግኖስቶ ቴዎ(Ἀγνώστῳ θεῷ) ብለው መስዋዕትን ያቀርባሉ[ሐዋ 17:23]። በሐዋርያት ስራ ም.17 ቁ.16-34 ላይ ያለውን ክፍል ስንመለከት ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የግሪክ መዲና በሆነችው በአቴና ሲዘዋወር ያገኘው ነገር ከተማውን የሞሉት የሚታወቁና የማይታወቁ የአማልክት መሰዊያዎችን ነበር። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በቁጥር 24 ላይ አንድ ወሳኝ ንግግርን በአርዮስፋጎስ አደባባይ ላይ ቆሞ ስለ ክርስትና አስተምህሮ ሰበከ። “ዓለሙንና በእርሱ ያለውን ሁሉ የፈጠረ አምላክ እርሱ የሰማይና የምድር ጌታ ነውና እጅ በሠራው መቅደስ አይኖርም፤”  — ሐዋርያት 17፥24 “ὁ θεὸς ὁ ποιήσας τὸν κόσμον καὶ πάντα τὰ ἐν αὐτῷ, οὗτος οὐρανοῦ καὶ γῆς ὑπάρχων κύριος οὐκ ἐν χειροποιήτοις ναοῖς κατοικεῖ.” (Πραξεις Αποστολων 17:24) በክፍሉ ላይ እርሱ ወይም ሆውቶስ/οὗτος የሚለው በባለቤትነት ሙያ(Nominative case) የመጣው ነጠላ መደብ ተውላጠ ስም እየገለጸ ያለው አምላክ(ቴዎስ/θεὸς) እና ጌታ(ኩርዮስ/κύριος) የሚለውን ስም ነው። ይሄ ደግሞ በክርስትና አስተምህሮት ውስጥ ነጠላ ምንነት ያለው አሐዳዊ አምላክ ወይም ጌታ እንዳለ ያሳያል። እግዚአብሔር አምላክ በምንነት ደረጃ(በስልጣን፣ አገዛዝ፣ በባህሪይ፣ በመፍጠር) አንድ ወይም ነጠላ አምላክ እንደሆነ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በአርዮስፋጎስ አደባባይ ለአቴና ሰዎች አጥብቆ ሲናገር እናስተውላለን። ይሄ ንግግር ደግሞ አስተምህሮተ ክርስትና(ሥላሴያውያን) አሕዳዊ የመለኮት አስተምህሮ(Monotheism) እንዳላቸው የሚያረጋግጥ ነው። በሚገርም ሁኔታ ደግሞ በንጽጽር መልኩ የአቴና ሰዎች መድብላዊ አማልክት (Polytheism) አምላኪዎች እንደሆኑ በቁጥር  23 ላይ ገልጾልን እንመለከታለን፦ “ የምታመልኩትን እየተመለከትሁ ሳልፍ፦ ለማይታወቅ አምላክ የሚል ጽሕፈት ያለበትን መሠዊያ ደግሞ አግኝቼአለሁና፦ እንግዲህ ይህን ሳታውቁ የምታመልኩትን እኔ እነግራችኋለሁ።”  — ሐዋርያት 17፥23 “διερχόμενος γὰρ καὶ ἀναθεωρῶν τὰ σεβάσματα ὑμῶν εὗρον καὶ βωμὸν ἐν ᾧ ἐπεγέγραπτο· Ἀγνώστῳ θεῷ. ὃ οὖν ἀγνοοῦντες εὐσεβεῖτε, τοῦτο ἐγὼ καταγγέλλω ὑμῖν.”(Πραξεις Αποστολων 17:23) የምታመልኩትን ከሚለው አማርኛ ይልቅ የበኩረ ቋንቋው(ግሪኩን) ይበልጡን መመልከቱ ጠቃሚ ነው። ምክንያቱም ” የምታመልኩትን” ብሎ የገባውታ ሴባስማታ ሁሞን(τὰ σεβάσματα ὑμῶν) የሚል የግሪኩ ሐረግ ነው። ሴባስማታ (σεβάσματα) የሚለውን የግሪክ ቃል ነጥለን ስንመለከተው የመጣው በቀጥተኛ ተሳቢ ሙያ(Accusative case) በብዙ ቁጥር አመልካች መደብ(plural form) በግዑዝ ጾታ(Neuter Gender) የገባ ሲሆን በቀጥታ ሲተረጎም የሚመለኩ ነገሮች የሚል ትርጓሜን ይሰጣል። ይህ ማለት ደግሞ ከላይ ለማየት እንደሞከርነው መድብለ አማልክት አምላኪዎች(Polytheists) እንደሚባሉ ተመልክተናል። ስለዚህ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በአቴና የሚገኙት ጣኦት አምላኪ ሰዎች መድብለ አማልክት አምላኪዎች (Polytheists) እንደሆነ እግረ መንገዱን ሲናገራቸው እንመለከታለን። በመጨረሻም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በክርስትናና በግሪካውያን መካከል ያለውን የነገረ መለኮት ልዩነት በግልጽ ሁኔታ አሳይቷል። ደግሞ እኛ ክርስቲያኖች የክርስትናችን አስተምህሮ በሥላሴ እምነተ አምድ ላይ የተመሰረተ ነው። በታሪክም ውስጥ ነብያት በብሉይ ሐዋርያት በአዲስ ኪዳን አስተምረው አልፈዋል። ቤተ ክርስቲያንም ይህን እውነት ተቀብላና አምና ስታስተምረውና ስትጠብቀው ቆይታለች። ሥላሴ የሚለው ቃል በራሱ የእግዚአብሔር የመለኮታዊ መገለጫ ስያሜ ነው። ሥላሴ የግእዝ ቃል ሲሆን ሠለስት ሦስት፤ ሠለሰ ሦስት ሆነ ማለት ሲሆን “ሥላሴ” ማለት ደግሞ ሦስትነት በአንድነት ማለት ነው።ይህም ማለት አንድ ሲሆን ሶስትነትም እንዳለው የሚያመለክት ነው። ይህም ደግሞ እግዚአብሔር በስም፣ በአካልና በግብር በሶስትነት የተገለጠ አምላክ ሲሆን በመለኮታዊ ስልጣን፣ በአገዛዝ፣ በባህሪ፣ በመፍጠርና በፍቃድ አንድ የሆነ አምላክ ነው። ስለዚህ አስተምህሮተ ሥላሴ ፈጽሞ ሥሉስ አማልክትን (Tritheism) የሚያሳይ አይደለም። በሥሉስ አማልክት (Tritheism) የሚያምኑት ሞርሞኖች (የመጨረሻው ዘመን ቅዱሳን) የጆሴፍ ስሚዝ ተከታዮች እንጂ ሥላሴያውያን አይደሉም። ስለ ሞርሞኖች በሰፊው በሌላ ጊዜ እንመለሳለን። ብዙ ለዘብተኛም ሆኑ አጥባቄያነ የነገረ መለኮት ሊቃውንት አስተምህሮተ ሥላሴን የአሕዳዊ የመለኮት አስተምህሮ እንደሆነ በጥናታቸው አረጋግጠውት እንመለከታለን። ለተጨማሪ ምንጮች፦ William F. Albright, From the Stone Age to Christianity; H. Richard Niebuhr; Monotheistic Religion resources; Kirsch, God Against the Gods; Woodhead, An Introduction to Christianity; The Columbia Electronic Encyclopedia Monotheism; The New Dictionary of Cultural Literacy, monotheism

አስተምህሮተ ሥላሴ አሕዳዊ ወይስ መድብላዊ? Read More »

Scroll to Top